ምሥጢረ ቁርባን

ቁርባን ፤ ማለት ፣ ለእግዚአብሔር የሚቀርብ አምኃ ፣ መስዋዕት ፣ መንፈሳዊ ነገር ሁሉ ማለት ሲሆን ፤ በዚህ ትምሕርታችን ግን ፤ ስለ ሐዲስ ኪዳን መስዋዕት (የክርስቶስ ሥጋና ደም) እንማራለን ።

በብሉይ ኪዳን ለሐዲስ ኪዳን ቁርባን (መስዋዕት) ምሳሌዎች

  • የመልከ ጼዴቅ መስዋዕት ዘፍ 14 18 ። ዕብ 5 6 ። ዕብ 6 1 ። ህብስቱ የሥጋው ፤ ወይኑ የደሙ ምሳሌ ፤ መልከ ጼዴቅ የክርስቶስ ፤ አብርሐም የምዕመናን ።

  • የእስራኤል ፋሲካ ። ዘፀ 12 1 ። ሞት የዲያብሎስ ፤ እስራኤል የምዕመናን ፤ በጉ የክርስቶስ ምሳሌ ።

  • የእስራኤል መና ። ዘፀ 16 13 ። መና የጌታችን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ፤ እስራኤል የምዕመናን ፤ ደመና የእመቤታችን

በብሉይ ኪዳን መስዋዕት ቁርባን ያቀረቡና በረከት ያገኙ አባቶች አዳም አባታችን አዳም ባቀረበው መስዋዕት ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን በኋላ ሰው ሆኖ እንደሚያድነው ቃል ገባለት ። ዘፍ 3 22 ። ገላ 4 4

  • ኖኅ ባቀረበው መስዋዕት ለኖኅና ለልጆቹ ምድርን ዳግም በመቅሰፍት እንደማያጠፋት በቀስተ ደመና ምልክት ቃል ገባላቸው ። ዘፍ 9 1 ። ዘፍ 9 8

  • አብርሐም ዘፍ 18 3 ። አባታችን አብርሐም ባቀረበው መስዋዕት በዘርህ አሕዛብ ሁሉ ይባረካሉ የሚለውን የተስፋ ቃል ሰማ ፤ ያም ዘር የተባለው ለጊዜው ይስሐቅ ሲሆን፤ ፍጻሜው ግን ለጌታ ነበር ።

  • መልከ ጼዴቅ ዘፍ 14 17 ። መዝ 109 4 ። ዕብ 5 6 ። በእግዚአብሔር ፊት ባቀረበው መስዋዕት ክህነቱ ለዘለዓለም ተብሎለት የክርስቶስ ምሳሌ ሆነ ። ዕብ 7 1

  • ዳዊት መዝ 131 11 ። መስዋዕት ባቀረበበት ሠዓት ከአብራክህ የተገኘው ልጅህ በዙፋንህ ይነግሣል ተባለለት ፤ ይህም ለጊዜው የተነገረው ለሰሎሞን ሲሆን ፍጻሜው ለክርስቶስ ነበር ። መዝ 71 1 ። ሌሎችም በእግዚአብሔር ፊት ንጹህ መስዋዕታ ቸውን እያቀረቡ በረከት ተቀብለዋል።

ምሥጢረ ቁርባን በሐዲስ ኪዳን

በብሉይ ኪዳን ዘመን ይቀርብ የነበረው የመስዋዕት ቁርባን ፤ ከበግ ፤ ከላምና ፤ ከተለያዩ እንስሳት ነበር ። በሐዲስ ኪዳን ግን እንስሳት በቤተ መቅደስ ውስጥ መስዋዕት (ቁርባን) ሆነው አይቀርቦም መስዋዕት ሁሉ በክስቶስ ሥጋና ደም ተጠቃሏል ። ይህንም የአዲስ ኪዳን መስዋዕት የመሠረተው ራሱ ጌታችን ሲሆን ፤ በጸሎተ ሐሙስ ማታ አስራ ሁለቱ ሐዋርያት እንዳሉ በመጀመሪያ መስዋዕተ ኦሪትን ሰርቶ ካሳለፈ በኋላ ኅብስቱና ወይኑን ባርኮ “ነገ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬና የሚፈሰው ደሜ ይህ ነው ብሉ ጠጡ ብሎ ሰጣቸው” ። ማቴ 26 26

ዛሬ ካህኑ ኅብስቱን በጻህል ወይኑን በጽዋ አድርጎ ጸሎተ ቅዳሴውን እየጸለየ.. ሲባርከው እንደዚያ ጊዜው ኅብስቱ ተለውጦ ሥጋ መለኮት ወይኑም ተለውጦ ደመ መለኮት ይሆናል ። ይህንም ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም በምንቀበልበት ጊዜ ለእኛ ሲል የተቀበለውን መከራና ስቃይ እያሰብን ራሳችንን በንስሓ ከኃጢአት ንጹህ አድርገን ከንስሓ የቀረውን በደላችንን እንደሚደመስ ስልን ፤ ከበደል እንደሚያነጻንና የዘለዓለም ሕይወት እንደሚሰጠን አምነን መሆን አለበት ።

1ቆሮ 11 23 “ይህንም ለመታሰቢያዬ አድርጉት ” የሚለው ቃል ሥጋውንና ደሙን በምንቀበልበት ጊዜ ስለሰው ልጆች ሲል በቀራንዮ አደባባይ የተበውን መከራና በልባችን ውስጥ የተሳለውን አምላካዊ ፍቅሩን እያስታወስን እንድንኖር ነው መታሰቢያ የሚለው ቃል የሚያመለክተው የማይረሳ ነገርን ነውና ። ገላ 31

ጌታችን ይህን ምሥጢር ከማሳየቱ (ከመመስረቱ) በፊት በዮሐ 6 25-8 ። “ሥጋዬን ካልበላችሁ ደሜንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም ሥጋዬን የበላ ደሜንም የጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው ። ሥጋዬ እውነተኛ መብል ደሜም እውነተኛ መጠጥ (ሕይወትን የሚሰጥ) ነው ” በማለት ስለምሥጢረ ቁርባን በስፋት አስተምሯል ።

የቅዱስ ቁርባን ጥቅም

  • ከዚህ ዓለም በሞት ብንለይም እንኳን በሰማያዊ መንግስት የማያልፈውን የዘለዓለም ሕይወት እናገኛለን ። ዮሐ 6 54

  • ለኃጢአታችን ስርየት (ፍጹም ድኅነት) እናገኛለን ። ማቴ 26 26

  • ከጌታችን ጋር ከቅዱሳንም ጋር ያለንን አንድነት እናረጋግጠጣለን ። 1 ቆሮ 10 17

ሥጋውን በስንዴ ደሙን በወይን ያደረገበት ምክንያት ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈጸም ነው

ትንቢት በልቤ ደስታ ጨመርሁ ከስንዴ ፍሬና ከወይን ፍሬ በዛ ። መዝ 4 7 ። ይህም ቃል እውነተኛና ፍጹም የሆነው ዘለዓለማዊ መድኃኒት ቅዱስ ቁርባን በስንዴና በወይን እንደሚደረግ ያመለክታል ።

ምሳሌ የክርስቶስ ምሳሌ፤ መልከ ጼዴቅ መስዋዕት የሚያቀርበው በስንዴና በወይን ስለነበረ ምሳሌውን ለመፈጸም ። ዘፍ 14 17

ሥጋውንና ደሙን በምግብ ያደረገበት ምክንያት

  • ምግብ ከሰውነት ጋር እንደሚዋሃድ ሥጋውንና ደሙን ስንቀበል በእውነት እንደሚዋሃደን ለማስረዳት።

  • ምግብ ለሥጋችን ኃይል እንደሚሆነን ሥጋውና ደሙም ለነፍሳችን መንፈሳዊ ኃይል ይሰጠናል።

  • አዳምና ሄዋን በምግብ የእግዚአብሔር ልጅነታቸውን እንዳስወሰዱ ፤ በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ ልጅነታችንን ሊመልስልን ። ዘፍ 3 1 ። ዮሐ 6 49

  • ቅዱስ ቁርባንን ፤ በበላችን ንስሓ ከገባን በኋላ ሁልጊዜ መቀበል ይገባናል ። የኃጢአታችን ስርየት የሚረጋገጠው በቅዱስ ቁርባን ነውና ። ማቴ 27 27

ምዕመናን በሕይወት እስካሉ ደረስ ወንድም ይሁን ሴት ፣ ታናሽም ይሁን ታላቅ ከቅዱስ ቁርባን መለየት የለባቸውም ይህ ምሥጢር በፆታ በዕድሜ የማይገደብ ለሁሉ የተሰጠ ነውና ። ዮሐ 6 54 ። በሰራነው ስህተት ተጸጽተን ንስሓ ሳንገባ በድፍረት ሥጋውንና ደሙን መቀበል የለብንም ፤ ይህን የሚያደርጉ ሰዎች ዕዳ አለባቸው ። 1ቆሮ 11 27 ። የምንቀበለው ቅዱስ ቁርባን ጌታችን በቀራንዮ አደባባይ ተሰቅሎ ከዋለ በኋላ ፤ ዘጠኝ ሰዓት ሲሆን በራሱ ሥልጣን ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው ለይቷል ። ዮሐ 10 18 ። ዮሐ 19 30 ። በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ሄዶ በዚያ የነበሩ ነፍሳትን ወደ ገነት ከመለሰ በኋላ ሶስት መዓልትና ሶስት ሌሊት በከርሠ መቃብር ከነበረው ሥጋ ጋር በፈቃዱ አዋህዶ ተነሳ ፤ በዚህ ጊዜ ውስጥ ግን(ሥጋውና ደሙ በተለያዩበት ወቅት) መለኮት ፣ ከነፍ ስም ከሥጋም ጋር አልተለየም ። 1ዼጥ ። ስለዚህ እኛ የምንቀበለው ሥጋና ደም ፤ ነፍስ የተለየችው መለኮት የተዋሃደው ነው ። 1ዼጥ 3 18

ዳውንሎድ ሞባይል አፕ

ሶሻል ሚድያ ላይ ያግኙን

 

Copyright © 2010 – 2023 zetewahedo.com | All rights reserved.
error: Content is protected !!
Scroll to Top