ስለ ምስጢረ ጥምቀት እና ስለ ጥምቀት በዓል አከባበር ከቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር የተደረገ ውይይት

ጠበል እና ጥምቀት

ጥምቀት ምንድነዉ?
ብዙ ሊቃውንት እንደሚስማሙበት ጥምቀት የግዕዝ ቃል ሲሆን “ውሃ ውስጥ መዘፈቅ” የሚል ትርጉም አለው። ይህ ነጠላ ትርጉሙ ሲሆን ምሥጢራዊ ትርጉሙ ደግሞ “በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም በውሃ ተጠምቆ ስመ ክርስትናን መቀበል” ነው። የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማናዊ ጥምቀት ከመጽሐፍ ቅዱስና ከእምነት አንጻር ሲታይ ሞታችን፣ መቀበሪያችን፣ ትንሣኤያችን በመሆኑ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ህብረት የሚፈጥርልን ምሥጢር ነው።
“ከክርስቶስ ጋራ አንድ ትኾኑ ዘንድ የተጠመቃችኹ ዅሉ ክርስቶስን ለብሳችዃልና።
አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም ዅላችኹ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችኹና” ገላ 3፥27
ጥምቀት በመረጨት ወይም በማፍሰስ የሚፈጸም ሰይሆን ሰውነት በሙሉ በማጥለም በሥላሴ ስም 3 ጊዜ ብቅ ጥልም በማለት የሚፈጸም ምሥጢር ነው።

የጥምቀት ምሳሌ
1. ግዝረት
2. የእስራኤል ቀይ ባሕርን ማቋረጥ
3. አብርሃም ባሕረ ዮረዳኖስን ተሻግሮ ለመልከጼደቅ ጽዋዕ በረከት ሕብስት አኮቴት ማቅረቡ
4. የኖሕ መርከብ

ጠበልምንድነዉ?

ጠበል ማለት ቃሉ የግዕዝ ሲሆን ትርጉሙም አፈር ( አቧራ) ማለት ነው ። ነገር ግን በቤተ ክርስቲያናችን ጠበል ብለን የምንጠራው በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ሕሙማን የሚፈወሱበት ተአምራት የሚደረግበት ቅዱስ ውሃ ማለት ነው።
ጠበል ማለት በግእዙ ቅዱስ ውሃ ማለት ከሆነ ሕሙማን የሚፈወሱበት ተአምራት የሚደረግበት ለምን አፈር ተባለ ቢሉ?መልሱ በዮሐንስ ወንጌል ላይ የሚገኘው ቃል ነው ÷
👉ዮሐ ምዕ 9÷6
ይህን ብሎ ወደ መሬት እንትፍ አለ በምራቁም ጭቃ አድርጎ በጭቃው የዕውሩን ዓይኖች ቀባና።
ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ አለው፤ ትርጓሜው የተላከ ነው። ስለዚህ ሄዶ ታጠበ እያየም መጣ። ይሕ ተአምር የተደረገው ሥጋን የተዋሐደው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምራቁ ለውሶ ጭቃ ባደረገው መሬትና በሰሊሆም መጠመቂያ ከሚገኘው ቅዱስ ውሃ ድብልቅ በመሆኑ ሕሙማን የሚፈወሱበት ቅዱስ ውሃ ተብሎ ተጠርቷል ።

ከጥምቀት ለክርስቲያኖች ምን ይገኝበታል
1. ጽድቅ ይገኝበታል። “ያመነ የተጠመቀ ይድናል።” ማር 16፥16
2. እንደገና እንወለድበታለን። ሁለተኛ ከእግዚአብሔር የምንወለድበት ረቂቅ ምሥጢር ነው፤ የሚፈጸመውም በውሃና በመንፈስ ነው። ከውሃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግስት አያይም። “ከውሃና ከመንፈስ ልትወለዱ ግድ አላችኹ” ዮሐ 3፥3 እንዲል። በክርስቶስ ክርስቲያን በወልድ ዉሉድ የሚያሰኝ ነው።
3. የኃጢአት ሥርየት ይገኝበታል። “ኃጢአታችሁ ይሠረይ ዘንድ ንስሐ ግቡ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሔር ስም ተጠመቁ።” ሐዋ 2፥3
4. ክርስቶስን እንመስልበታለን። አርዓያ ሆኖ ያሳየንን በመፈጸም በሥራ እንመስለዋለን። “ከክርስቶስ ጋራ አንድ ትኾኑ ዘንድ የተጠመቃችኹ ዅሉ ክርስቶስን ለብሳችዃልና።” ገላ 3፥27። “ወይስ ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋራ አንድ እንኾን ዘንድ የተጠመቅን ዅላችን ከሞቱ ጋራ አንድ እንኾን ዘንድ እንደ ተጠመቅን አታውቁምን፧” ሮሜ 6፥3
5. አድስ ሕይወት ይገኝበታል። “እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በዐዲስ ሕይወት እንድንመላለስ ፥ከሞቱ ጋራ አንድ እንኾን ዘንድ በጥምቀት ከርሱ ጋራ ተቀበርን። ሮሜ 6፥4

ጥምቀት በመፅሐፍ ቅዱስ

1. የብሉይ ኪዳን አባቶች በዓላቸውን ከማክበራቸው በፊት በውሃ በመረጨት በመነከርና በመጥለቅ ይነጹ ነበር። የዝግጅቱ ዕቃዎችንም በውሃ ማንጻት አለባቸው ከርኩሰት መንጻት በዚህ ነበርና። ዘሌ 6፥27
2. ኢዮብና ንዕማን በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቀው ተፈውሰዋል። 2ነገ 5፥8
3. ለ 38 ዓመት አልጋ ቁራኛ የነበረው ሰው እንደመሰከረው በሰሊሆም ቤተሳይዳ ውኃ ሰዎች እየተጠመቁ ፈውስ ያገኙ እንደነበረ እርሱ ግን ወደ ውኃው የሚወስደው በማጣቱ በዚያ እንዳለ ለጌታ መንገሩ ሌላው ማስረጃ ነው። ዮሐ 5፥2
4. በዚያን ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ከገሊላ ክፍል ከናዝሬት ወደ ዮርዳኖስ መጣ። ማር 1፥9።

ስለ ጠበል መፅሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎችን ስንመለከት
👉2ኛ ነገ ምዕ 5÷1-15
👉ዮሐ ምዕ 5÷2-5
👉ሕዝ ምዕ 36÷25
መናፍቃን በጠበል ላይ የሚያነሱትን ጥያቄ ስናይ ደግሞ ለምን ጠበሎች በቅዱሳን ስም ይሰየማሉ?አዳኙ እግዚአብሔር ሆኖ ሳለ ለምን የድንግል ማርያም ጠበል: የቅዱስ ሚካኤል :የቅዱስ ገብርኤል ጠበል ወዘተ….. ተብሎ ተሰየመ? ቢሉ መልሱ ግልፅ ነው
የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም:የቅዱሳን መላእክት የፃድቃን ሰማዕታት የነቢያት ሐዋርያት እና የሁሉም ቅዱሳን ክብራቸው ይገለጥ ዘንድ, መታሰቢየቸው ይሆን ዘንድ እንዲሁም ረድኤት በረከታቸው ለኛ ይሆን ዘንድ ጠበሎች በቅዱሳን ስም ይሰየማሉ ። መፅሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎችን ስንመለከት
👉ምሳሌ 10÷7
👉ኢሳ 56÷4-6

ስለዚሕ ጠበል(አፈር) ከጥንትም የነበረ አሁንም ያለ ወደፊትም ሕሙማንን እየፈወሰ ተአምራትን እያደረገ የሚኖር የተቀደሰ ውሃ ነው ።

ጠበል ምንድን ነው?

ጠበል ማለት በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ሕሙማን የሚፈወሱበት ተአምራት የሚደረግበት ቅዱስ ውኃ ነው::
ኦርቶዶክስዊ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሚገባ..ንዕማን ለምጻም እንደነበር እና በጠበል ኃይል እንደዳነ መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምረናል “ንዕማንም በፈረሱና በሰረገላው መጣ፥ በኤልሳዕም ቤት ደጃፍ ውጭ ቆመ። ኤልሳዕም ሂድ፥ በዮርዳኖስም ሰባት ጊዜ ታጠብ፤ ሥጋህም ይፈወሳል፥ አንተም ንጹሕ ትሆናለህ…… ወረደም፥ የእግዚአብሔርም ሰው እንደ ተናገረው በዮርዳኖስ ሰባት ጊዜ ብቅ ጥልቅ አለ፤ ሥጋውም እንደ ገና እንደ ትንሽ ብላቴና ሥጋ ሆኖ ተመለሰ፥ ንጹሕም ሆነ።”2ነገስ. 5፡1-19
እንዲሁም ክርስቶስ በ ዮሐንስ 9:1-8″ኢየሱስ ይህን ብሎ ወደ መሬት እንትፍ አለ በምራቁም ጭቃ አድርጎ በጭቃው የዕውሩን ዓይኖች ቀባና። ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ አለው… ስለዚህ ሄዶ ታጠበ እያየም መጣ።
ክርስቶስ በቃሉ ብቻ ዐይንህ ይብራልህ ብሎ ማዳን ይችላል ግን በብሉይ ኪዳን ሕመምተኞች ይፈወሱበት ተአምራት ይደረግበት የነበረው ጠበል በሐዲስ ኪዳንም የተባረከና ፈቅዶ የሰጠን ጸጋ መሆኑን ለማስረዳት “ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ” አለው፡፡
ታዲያ ጠበሎች ሁሉ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መጠራት ሲኖርባቸው ለምን የማርያም ጠበል፤የሚካኤል ጠበል ፤የጊዮርጊስ ጠበል ይባላል የሚሉ መናፍቃን ? ይኸውም በጠበሉ ቅዱሳን እንዲታሰቡበት ነው
“እግዚአብሔር ሰንበቴን ስለሚጠብቁ ደስ የሚያሰኘኝንም ነገር ስለሚመርጡ ቃል ኪዳኔንም ስለሚይዙ ጃንደረቦች እንዲህ ይላልና። በቤቴና በቅጥሬ ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያና ስም እሰጣቸዋለሁ፤ የማይጠፋም የዘላለም ስም እሰጣቸዋለሁ።”(ኢሳይያስ 56:4-5 )

እንዲሁም “የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው” (ምሳሌ 10:7) በሚለው መጽሐፍ ቅዱሳዊ መረጃ መሰረት በጠበሉ ቅዱሳኑ መጠራታቸው መታሰቢያቸው እንዲሆን ነው፡፡ጠበሉን የፈጠረው መድኃኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን እና በጠበሉም አድሮ ሕሙማንን የሚፈውሰው እና ተአምራትን የሚያደርገው የእግዚአብሔር ኃይል መሆኑን በደንብ እናውቃለን፡፡
የኢትዮጵያኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስተያንያን ለሁሉም ጥያቄ መልስ አላት፣ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የቀደመችው እውነተኛይቱ መንገድ!(ኤርምያስ6:16) ለእኛ ለምናምነው ጠበሉን በእምነትና በንጹሕና በፈሪሃ እግዚአብሔር ከተጠቀምንበት ፈውስ እንደሚሆነን አንጠራጠም።ጠበሉ ሁላችንን ከሥጋዊና ከመንፈሳዊ ደዌ ይፈውሰናል፡፤

ምንጭ:-የመምህር ተመስገን ዘገዬ እይታዎች

ጠያቂ፡-ጠበል ምንድን ነው?

ጠበል ማለት በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ህሙማን የሚፈወሱበት ተአምራት የሚደረጉበት ቅዱስ ውሃ ነው::

ጠያቂ፡–መጽሀፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ አለ?

በሚገባ..ንዕማን ለምጻም እንደነበር እና በጠበል ሐይል እንደዳነ መጽሃፍ ቅዱስ ያስተምረናል “ንዕማንም በፈረሱና በሰረገላው መጣ፥ በኤልሳዕም ቤት ደጃፍ ውጭ ቆመ። ኤልሳዕም ሂድ፥ በዮርዳኖስም ሰባት ጊዜ ታጠብ፤ ሥጋህም ይፈወሳል፥ አንተም ንጹሕ ትሆናለህ…… ወረደም፥ የእግዚአብሔርም ሰው እንደ ተናገረው በዮርዳኖስ ሰባት ጊዜ ብቅ ጥልቅ አለ፤ ሥጋውም እንደ ገና እንደ ትንሽ ብላቴና ሥጋ ሆኖ ተመለሰ፥ ንጹሕም ሆነ።”2ነገሥት 5፡1-19
እንዲሁም ክርስቶስ በ ዮሐንስ 9:1-8 “ኢየሱስ ይህን ብሎ ወደ መሬት እንትፍ አለ በምራቁም ጭቃ አድርጎ በጭቃው የዕውሩን ዓይኖች ቀባና። ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ አለው… ስለዚህ ሄዶ ታጠበ እያየም መጣ። ክርስቶስ በቃሉ ብቻ አይንህ ይብራልህ ብሎ ማዳን ይችላል ግን በብሉይ ኪዳን ህመምተኞች ይፈወሱበት ፣ተአምራት ይደረግበት የነበረው ጠበል በሐዲስ ኪዳንም የተባረከና ፈቅዶ የሰጠን ጸጋ መሆኑን ለማስረዳት “ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ” አለው፡፡

ጠያቂ ፡— ታዲያ ጠበሎች ሁሉ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም መጠራት ሲኖርባቸው ለምን የማርያም ጠበል፤የሚካኤል ጠበል ፤የጊዮርጊስ ጠበል ይባላል?

መልሱ አጭር ነው ይኸውም በጠበሉ ቅዱሳን እንዲታሰቡበት ነው

ጠያቂ ፡–መጽሀፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ አለ?

አዎ በሚገባ ..ቅድስት ቤተክርስትያን ሁሉ ነገሯ መጽሀፍ ቅዱሳዊ ነው “እግዚአብሔር ሰንበቴን ስለሚጠብቁ ደስ የሚያሰኘኝንም ነገር ስለሚመርጡ ቃል ኪዳኔንም ስለሚይዙ ጃንደረቦች እንዲህ ይላልና። በቤቴና በቅጥሬ ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያና ስም እሰጣቸዋለሁ፤ የማይጠፋም የዘላለም ስም እሰጣቸዋለሁ።”(ኢሳይያስ 56:4-5 ) እንዲሁም “የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው” (ምሳሌ 10:7) በሚለው መጽሀፍ ቅዱሳዊ መረጃ መሰረት በጸበሉ ቅዱሳኑ መጠራታቸው መታሰቢያቸው እንዲሆን ነው፡፡ጠበሉን የፈጠረው መድሐኒአለም ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን እና በጠበሉም አድሮ ህሙማንን የሚፈውሰው እና ተአምራትን የሚያደርገው የእግዚአብሔር ሐይል መሆኑን በደንብ እናውቃለን፡፡

የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን በተወለደ በ30 ዘመኑ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በ5531 ዓ.ም በዘመነ ሉቃስ ጥር 11 ቀን ማክሰኞ ሌሊት 10 ሰዓት ተጠመቀ። ፍት.ነገ አን.19፤ ድስቅ፣ 29 ፤ ሉቃ. 3፣23

መጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በሚያስተምርበት ጊዜ ቃሉን የሰሙትን ሰዎች ያጠምቃቸው ነበር። “በምድረ በዳ እያጠመቀ የንስሐንም ጥምቀት ለኃጢአት ስርየት እየሰበከ መጣ። የይሁዳም አገር ሁሉ የኢየሩሳሌምም ሰዎች ሁሉ ወደ እርሱ ይወጡ ነበር ኃጢአታቸውንም እየተናዘዙ በዮርዳኖስ ወንዝ ከእርሱ ይጠመቁ ነበር።” ማር 1፥3

“ወሀሎ ዮሐንስ ያጠምቅ በገዳም” ዮሐንስ በምድረ በዳ ያስተምር ነበር። ወይሰብክ ጥምቀተ ለንስሐ ወይትኃደግ ሎሙ ኃጢአቶሙ” ኃጢአታቸው ሊሠረይላቸው የንስሐ ጥምቀትን ያስተምር ነበር።
“ወአሜሃ መጽአ እግዚእ ኢየሱስ እምገሊላ ውስተ ዮርዳኖስ ከመ ይጠመቅ እም ዮሐንስ” ማር 1፥9። በዚያን ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ከገሊላ ክፍል ከናዝሬት ወደ ዮርዳኖስ መጣ። “ወአጥመቆ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ” ዮሐንስ በዮርዳኖስ ወንዝ አጠመቀው። በመጠመቁ ጸጋ ሊያገኝበት አልነበረም ለጥምቀት ክብር ሊሰጥ እንጅ። “ወመጽአ ቃል እምሰማይ ዘይብል አንተ ውእቱ ወልድዬ ዘአፈቅር ወኪያከ ሠመርኩ።”፤”ደስታዬን የማይብህ የምወድህ ልጄ አንተ ነህ” የሚል ድምጽ ከወደ ሰማይ ተሰማ። ጌታችን ሲጠመቅ የባሕርይ አባቱ አብ “ዝንቱ ውእቱ ወልድዬ” ብሎ ሲመሰክር “መንፈስ ቅዱስ በአምሳለ ርግብ ወርዶ ከራሱ ላይ በመቀመጥ” አንድነቱ ሦስትነቱ ተገለጸ።

ጌታችን ለምን ተጠመቀ?

1. ዲያብሎስ በዮርዳኖስ ወንዝ ደብቆት የነበረውን የእዳ ደብዳቤያችንን ለመደምሰስ።
2. በጥምቀት ዳግም ልደት እንዳለን ለማጠየቅ አርአያ ሊሆነን።
3. ትሕትናን ለማስተማር። በአገልጋዩ በዮሐንስ መጠመቁ ትሕትናን ሊያስተምረን ነው።
4. አንድነቱንና ሦስትነቱን ለመግለጽ (“ሰማያት ተከፈቱ” ለሚለው አነጋገር መልስ ሊሰጥ)
5. ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ። በዮርዳኖስ ወንዝ እንደሚጠመቅ ትንቢት ተነግሮ ነበርና። መዝ 113፥3

ጥምቀት ሦስት አይነት ሲሆን አንደኛው በደም ጥምቀት ነው። ኢአማንያን ወደ ማመን በሚመለሱበት ጊዜ ለሚስጥረ ጥምቀት
ሳይደርሱ ለምን ወደ ክርስትና ገባችሁ ብለው
አሕዛብና ክፉዎች ቢገድሏቸውና ስሙን መስክረው ስለስሙ ቢሞቱ የፈሰሰው ደማቸው ጥምቀት ይሆንላቸዋል። (ለምሳሌ ፍያታዊ ዘየማን) ሁለተኛው በመንፈስ ቅዱስ መጠመቅ ሲሆን እግዚአብሔር ለመረጣቸውና ለፈቀደላቸው እንደ ሐዋርያት ጥምቀት አይነት ነው። ሐዋ 2፥3 ሦስተኛው ደግሞ ጌታችን የተጠመቀውና አርዓያ የሆነልንና እኛ የምንጠመቀው የውሃ ጥምቀት ነው።
ጥምቀት ሦስት ወገን ነው። አንደኛ የአይሁድ ሁለተኛ የዮሐንስ ሦስተኛ የጌታ ጥምቀት ናቸው።

ታቦታቱ ወደ ባሕር መውረድ

ይህ በዓል በሚከበርበት ጊዜ ዋዜማው “ከተራ” ይባላል። ከተራ ማለት መገደብ ማለት ነው። በዚህ ቀን ታቦታት ከየቤተክርስቲያናቸው ወጥተው በወንዝ ዳር ወይም በሰው ሰራሽ የውሃ ግድብ በዳስ በድንኳን ያድራሉ። ታቦታቱ ወጥተው ውሃ ወዳለበት መሄዳቸው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአገልጋዩ በዮሐንስ ዕጅ ሊጠመቅ በወደደ ጊዜ ሁለቱም በአድነት ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ በመውረዳቸው ነው። ቤተክርስቲያን ይህንን ዓቢይ ምስጢርና ሥርዓት ተከትላ ታቦታቱን ከመንበራቸው አውጥታ፤ የውሃ ምንጭ፤ ወዳለበት ወንዝ በመውረድ በልዩ ልዩ መንፈሳዊ ሥርዓት በዓሉን ታከብራለች። ተከታዮቿ ምዕመናንም ታቦታቱን አጅበው አብረው በመውረድ በዓሉን በደመቀ ሁኔታ እያከበሩ የበረክቱ ተሳታፊ ይሆናሉ።

የህፃናት ጥምቀት

የሕፃናት የ40 ቀንና የ80 ቀን ጥምቀት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ለሚስጥረ ጥምቀት አፈጻጸም ብርቱ ጥንቃቄ ታደረጋለች፡፡ ሰው ሁሉ በጥምቀት አማካኝነት የሚሰጠውን ጸጋ እንዲያገኝ አሰፈላጊውን ጥረት ሁሉ ትፈጽማለች፡፡ ሰዎች ሳይጠመቁ እንዳይሞቱ በማለት ሕጻናትን የምታጠምቀው በቅዱሳት መጸሕፍት በተረዳችው መሠረት እንደሆነ ከዚህ ቀጥለን ለማየት እንሞክራለን፡፡
መጽሐፈ ኩፋሌ፡- 4፡9 ከተፈጠረባት ምድር ለአዳም አርባ ቀን ከተፈጸመለት በኃላ ይገዛትም ይጠብቃትም ዘንድ ወደ ገነት አሰገባው፡፡ ሚስቱንም በሰማንያ ቀን አሰገባት፡፡
ይላልና ለአዳምና ለሔዋን ንጹሕ ጠባይዕ ሳይድፍባቸው ከመንፈስ ቅዱስ የጸጋ ልጅነት ተቀብለው በ40ና በ80 ቀን ገነት እንድገቡ ዛሬም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር መጀመረያ በሠራው ሥራዓት መሠረት በአዳም አለመታዘዝ ምክንያት የተወሰደውን ልጅነት ለማሰመለሰ ሕጻናት ወንዶችን በ40 ቀን ሕፃናት ሴቶችን በ80 ቀን ዕድሜያቸው ታጠመቃለች፡፡
ሀ. ሕጻናት የዘላለምን ሕይወት እንዲያገኙ ወላጆቻቸውና ቤተ ክርስቲያን የሚሹት ነው፡፡
የሐ ፡- 3፡5 ሰው ከወኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግስት ሊያይ አይችልም፡፡
ስለዚህ ሕጻናት በወላጆቻቸው እምነት የተነሳ የወላጆቻቸውን እምነት የእነርሱ እምነት በማድረግ ገና በሕጻንነት ጊዜያቸው ከእግዚአብሔር መንግስት ውጭ እንዳይሆኑ ታጠምቃቸዋለች፡፡ ዳሩ ግን ሳይጠመቁ ቢሞቱ ጌታ እንደተናገረው መንግስተ ሰማይን አያዩአትም፡፡
እንደ ጌታ ትምህርት የሚንሄድ ከሆነ ሰው ብሎ ባጠቃላይ ሕጻናትን አዋቂዎችን ሁሉ ጨምሮ ተናገረ እንጂ ከሕጻናት በሰተቀር አላለም፡፡ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግስት ሊያይ አይችልም፡፡
ለ. ሕጻናት በመጠመቃቸው የቤተ ክርስቲያን አባል ስለሚሆኑ የእግዚአብሔር ጸጋ ተካፋዮች ይሆናሉ፡፡
ገና ከሕጻንነታቸው ጀምሮ የቤተ ክርስቲያንን ሕይወት ይለማመዳሉ፡፡ በዚህ ፈንታ ከሕጻንነታቸው ጊዜ ጀምረው ከእግዚአብሔር ጸጋ ተራቁተው የሚያድጉ ከሆነ ለመጥፎ ሕይወት ይዳረጋሉ፡፡
ሐ. ለሕጻናት በሚደረግ ጥምቀት መጽሐፍ ቅዱስ አይቃወምም እንደውም ይደግፋል፡፡
ማር ፡- 10፡14 ሕጻናትን ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ተዉ አትከልክሉአቸው
እንዲሁም ጌታችን ያመነ የተጠመቀ ይድናል ሲል በዚያን ዘመን ገና ወንገል መሰበክ በጀመረበት ላሉት ሰዎች የተነገረ ሲሆን ከክህደታቸውና ከጥርጥራቸው ተመልሰው የሚመጡ ሁሉ አምነው መጠመቅ እንዳለባቸው የሚያሰገነዝብ ነው፡፡ ሕጻናት የእግዚአብሔር ልጆች ሊሆኑ እንደሚገባ ጌታችን ሲገልጽ
ማቴ ፡- 19፡14 ሕጻናት ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ተዉአቸው አትከልክሏቸው መንግሰተ ሰማያት እንደ እነርሱ ላሉት ናትና ብሏል፡፡ በዚህ የጌታ ትምህርት መሠረት ቤተ ክርስቲያንም የመረዋንና የመሥራችዋን የክርስቶስን መርሕ በማድረግ ወላጆቻቸው ታቅፈው ወደ ቤተ ክርስቲያን ይዘው በመምጣት ተጠምቀው የእግዚአብሔር ልጆች የቤተ ክርስቲያን አባላት እንዲሆኑ ሲያደረጉ እርሷ ከልካይ አትሆንም፡፡
ጌታ ተዉአቸው ይምጡ ልጅነትን ፤ ጸጋን፤ በረከቱን ያግኙ ብሏልና፡፡
ሕፃናት ንጹሐነ አእምሮ መሆናቸውን ጌታ ሲያሰተምር እንደ ሕፃናት ካልሆናችሁ መንግሰተ ሰማይ አትገቡም ብሏል፡፡
መ. መጽሐፍ ቅዱስ ሕፃናት መጠመቃቸውን ያሰተምረናል፤
1. ሐዋ ፡- 16፡33 በእሥር ቤቱ በተደረገው ተአምር የተደነቀውና ወደ ክርስትና እምነት የተሳበው የወኀኒ ጠባቂ ጳውሎስና ስላስ ካሰተማሩትና ካሳመኑት በኋላ ከነቤተሰቡ መጠመቁ ተገልጾአል፡፡ እንግዲህ የተሰበከውና ያመነው የወኀኒ ጠባቂው ስሆን የተጠመቁት ግን ሕፃናትን ጨምሮ መላው ቤተሰቡ ነው፡፡
2. ሐዋ ፡- 16፡15 ልብዋን ጌታ የከፈተላትና ቃሉን አድምጣ ሕይዋትውን ለክርስቶስ የሰጠችው ልድያ ባመነች ጊዜ የተጠመቀችው ብቻዋን ሳይሆን ከመላው ቤተሰብዋ ጋር ነው፡፡ ከቤተሰቡ መካከል ሕፃናት መኖራቸው የማይቀር ነው፡፡
3. 1ቆሮ ፡- 1፡16 ቅዱስ ጳውሎስ የእስጢፋኖስንም ቤተሰቦች ደግሞ አጥምቄያለሁ በማለት የእስጢፋኖስን መላ ቤተሰብ ማጥመቁን ገልጾአል፡፡ እንዚህ የእስጢፋኖስ ቤተሰቦች ሁሉ ትልልቆች ብቻ ናቸውን? ሕጻናት የሉበትም ይሆን?
4. ሐዋ.ሥራ 2 ላይ እንደተገለጸው በበዓለ ሃምሳ ከ3000 ያላነሱ ሰዎች በጴጥሮስ ተሰበኩ፡፡ ከእንዚያ ውስጥ ብዙዎቹ መጠመቃቸው ተገልጸዋል፡፡ የተጠመቁት ግን አዋቂዎች ብቻ መሆናቸውን የሚገልጽ ቃል የለም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሕጻናትን ጥምቀት የሚነቅፍ ባንዱም ክፍል ተጽፎ አናገኝም፡፡
እስከ አሁን እንደተገለጸው መጽሐፍ ቅዱስ የሕፃናትን ጥምቀት ያልነቀፈ ሲሆን በብሉይ ኪዳን የጥምቀት ምሳሌ የነበሩትን ስንመለከት ይበልጥ የሕጻናትን ጥምቀት ትክክልኛነት ያረጋግጡልናል፡፡
ግዝረት የጥምቀት ምሳሌ ነው፡፡ ሕፃናት በተወለዱ በስምነተኛው ቀን ይገረዙ ነበር፡፡ (ዘፍ ፡- 17፡12)፡፡
እንግዲህ ሕፃናቱ የሚገረዙት በወላጆቻቸው እምነት እንጅ እነርሱ ዐውቀው ግረዙን ብለው አይደለም፡፡ የእስራኤል ቀይ ባሕርን ማቋረጥ የጥምቀት ምሳሌ መሆኑ በ1ቆሮ 10፡2 የተገለጸ ስሆን ባሕሩን ያቋረጡት ዐዋቂዎች ብቻ ሳይሆኑ ሕፃናትም ጭምር ናቸው፡፡ ከባርነት ከፈርዖን አገዛዝ ነፃ የወጡት ሕፃናቱም ጭምር ናቸው፡፡ እስራኤል ከቡኩረ ሞት የዳኑበት የአንድ አምት ጠቦት በግ ደግሞ ምሳሌነቱ የጌታ መሆኑ የተወቀ ስሆን በዚያን ጊዜ በበጉ ደም አማካኝነት ከሞት የዳኑት የታዘዙትን እሺ ብለው የፈጸሙት ዐዋቂዎች ብቻ ሳይሆኑ የእነርሱም ልጆቹም ጭምር ናቸው፡፡ እንግዲህ በወላጆቻቸው እምነት ሕፃናቱ መዳናቸውን ልናሰተውል ይገባል፡፡
ስለዚህ ሕፃናት በአእምሮ ባለበሰሉበትና ስለጥምቀታቸው አምነው ተቀብያዋለሁ ሳይሉ የሚደረገው ጥምቀት እውነተኛ ጥምቀት አይደለም የሚሉ በእግዚአብሔር ቃል መሠረት ከላይ እንደተገለጸው ሁሉ መሳሳታቸው የተረጋገጠ ነው፡፡
እግዚአብሔር ሰውን ይመረጣል እንጂ ሰው እግዚአብሔርን አይመርጥም፡፡ ራሱ ባለቤቱ እንዳሰተማረው ሁሉ እኔ መረጥኋችሁ እንጂ እናንተ አልመረጣችሁኝም ብሏል (ዮሐ. 15፡16)፡፡ ድኀነት በእግዚአብሔር ቸርነት የሚገኝ እንጂ በሰው ትምህርት እና እውቀት የሚሸመት ወይም የሚገበይ ዕቃ አይደለም፡፡
ስለሆነም ቤተ ክርስቲያናችን ሕፃናትን ማጥመቋ ከመጽሐፍ ቅዱስና ከቀደሙት አበው ባገኘችው ትምህርት መሠረት ነው፡፡

ዳውንሎድ ሞባይል አፕ

ሶሻል ሚድያ ላይ ያግኙን

 

Copyright © 2010 – 2023 zetewahedo.com | All rights reserved.
error: Content is protected !!
Scroll to Top