ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ማለት ምን ማለት ነው

ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ (Orthodox Miaphysite)

ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ማለት ኢየሱስ ክርስቶስ በተዋህዶ ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ፣ ከሁለት አካል አንድ አካል ሆነ (ሥግው ቃል ነው) ብላ የምታምን ቀጥተኛና ትክክለኛ እምነት/ሃይማኖት ማለት ነው፡፡

– ሁለት አካላት የተባሉተ አካል መለኮትና አካለ ሥጋ ናቸው።
– ሁለቱ ባህርይ የተባሉትም ባሕርየ መለኮትና ባሕርየ ሥጋ ናቸው።

ኦርቶዶክስ (Orthodox)

“ኦርቶዶክስ” የሚለው ቃል የግሪክ ቃል ሲሆን የተቀናበረው “ኦርቶ” እና “ዶክስ” ከሚሉት ሁለት ቃላት ነው፡፡

ትርጉማቸውም ኦርቶ ማለት ቀጥተኛ: ትክክለኛ ማለት ሲሆን ዶክስ ማለት ደግሞ እምነት/ሃይማኖት ማለት ነው፡፡ በአንድነት ሲሆኑ ኦርቶዶክስ ማለት ቀጥተኛ፡ ትክክለኛ እምነት/ሃይማኖት ማለት ነው፡፡

ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ አገልግሎት ላይ የዋለው በ325 ዓ.ም በኒቅያ ጉባዔ ነው፡፡

በኒቅያ “ወልድ ፍጡር ነው” የሚለውን የአርዮስን የክህደት ትምህርት ለማውገዝና ሃይማኖታቸውን ለማፅናት የተሰበሰቡ ሃይማኖታቸው የቀና 318ቱ ሊቃውንት ይህን ቃል የተጠቀሙት ሐዋርያት ያስተማሯት ሃይማኖት ቀጥተኛና ትክክለኛ ናት ለማለት ነው፡፡

ሌሎች እንደ አርዮስ ክህደት ያሉት በየዘመኑ የሚነሱት ልዩ ልዩ አዳዲስ ትምህርቶች የምንፍቅና መሆናቸውን ለማረጋገጥ ይህችን ሃይማኖት ኦርቶዶክስ ብለዋታል፡፡
ተዋሕዶ (Miaphysite)

ተዋሕዶ የሚለው ቃል ከልሣነ ግእዝ የመነጨ ቃል ነው፡፡ ትርጒሙም “አንድ ሆነ” ማለት ነው።በዚህ ትርጉም ውስጥ አንድ የሆኑት መለኮታዊና ሰብዓዊ ባሕርይ (መለኮትና ትስብዕት) ናቸው፡፡ በዚህም መሠረት የተዋሕዶ ትርጓሜ በአጭሩ “ወልድ ዋሕድ” የሚለው ነው፡፡ክርስቶስ ሰው የሆነው ያለሚጠት (ያለመመለስ)፣ ያለ ውላጤ (ያለ መለወጥ)፣ ያለ ቱሳኤ (ያለ መቀላቀል)፣ ያለትድምርት (ያለ መደመር)፣ ያለ ቡዓዴ (ያለመለያየት)፣ ያለ ኅድረት (ያለ ማደር) ነው፡፡

ክርስቶስ ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ፣ ከሁለት አካል አንድ አካል የሆነው በተዋህዶ ነው፡፡ ስለዚህ ተዋሕዶ የሚለው ቃል ክርስቶስ ሰው የሆነበትን ምስጢር የሚገልፅ ታላቅ ቃል ነው፡፡ ክርስቶስ ሰው የሆነው በተዋሕዶ ነው

የተዋሕዶ ምሳሌዎች (Examples of Miaphysite)

የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ፡- ነፍስና ሥጋ ተዋሕደው አንድ ሰው ይባላል እንጂ ሁለት አይባልም፡፡

የብረትና የእሳት ተዋህዶ፡- ብረት በእሳት ሲግል የጋለ ብረት እንጂ ይህ ብረት ነው፣ ይህ ደግሞ እሳት ነው ተብሎ አይለይም፡፡

የሲና ሐመልማል፡- እሳቱ ሐመልማሉን ሳያቃጥለው፣ ሐመልማሉም እሳቱን ሳያጠፋው በአንድነት (በተዐቅቦ) መታየታቸው የተዋህዶ ምሳሌ ነው (ዘፀ 3፡2)፡፡

ዳውንሎድ ሞባይል አፕ

ሶሻል ሚድያ ላይ ያግኙን

Copyright © 2010 – 2026 zetewahedo.com | All rights reserved.
error: Content is protected !!
Scroll to Top