አሠርቱ ቃላት እና ስድስቱ ቃላተ ወንጌል

አሠርቱ ቃላት እና ስድስቱ ቃላተ-ወንጌል

ሕግጋተ እግዚአብሔር

  1. ሕገ ልቦና (የሕሊና ሕግ):-

  2. አሠርቱ ቃላት: /አሠርቱ ትዕዛዛት/ /አሠርቱ ሕግጋት/ /ሕገ መጽሐፍ (ሕገ ኦሪት)/:-

  3. ስድስቱ ሕግጋት /ስድስቱ ትዕዛዘተ / /ስድስቱ ቃላተ/ ወንጌል:-

  4. አሥሩ አንቀጸ ብፁዓን:-

  5. በለተ ምጽአት ከጌታችን የምንጠየቃቸውና የምንመልሳቸው 6 ጥያቄዎች:-

ከላይ በተራ ቁጥር የተዘረዘሩ ሕግጋት ማብራሪያ ተሰቶባቸዋል አንብበው ይጠቀሙ:+

+እግዚአብሔር አማላክ ፈጣሪ እንደመሆኑ ፈቃዱ የማይለወጥ ቀዋሚ ስለሆነ ጊዜያዊና ቅጽበታዊ ፍጥረት አልፈጠረም: ፈጥሮም ያለዓላማ: ያለሕግ ያለሥርዓት አልተወም።

በዓለሙ ሙሉ የሆነ እግዚአብሔር ሕግጋቱም ሁሉን የሚመለከትና ለዓለሙ ሁሉ ቀዋሚ የሆኑ ሕግጋት ናቸው። እነዚህም:- ሕገ ልቦና (የሕሊና ሕግ) : አሠርቱ ቃላት: ስድስቱ ቃላተ ወንጌል ናቸው።

+++++++

።።1።። ሕገ ልቦና (የሕሊና ሕግ):-

በሰው ልቦና አንድ ጊዜ ከተጻፈ ሳያረጅ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ የሚኖር ሕግ ነው። ሕገ ልቦና በሰው ሁሉ ልብ የሚገኝ እያንዳንዱን ሰው ማንም ሳያስተምረው: ክፉውንና ደጉን ለይቶ ሳይነግሩት እንዲያውቅ የሚያደርገው ነው። እውነተኛ ሰው ምንም ባይማር በዚህ በሕገ ልቦና ወይም በሕገ ተፈጥሮ መሰረት እውነትን ከሐሰት: ጽድቅን ከኃጢአት: ደጉን ከክፉ ለይቶ ያውቃል። ከዚህም የተነሣ እውነቱን ይናገራል: ይሰራል ከክፉም ይርቃል።

+። ስለ ሕገ ተፈጥሮ (ሕገ ልቦና) ቅዱሳት መጽሐፍት በተለያየ መንገድ ይመሰክራሉ። ስለዚህም ሐዋሪያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ አለ:-

፤ እግዚአብሔር ለሰው ፊት አያዳላምና።

፤ ያለ ሕግ ኃጢአት ያደረጉ ሁሉ ያለ ሕግ ደግሞ ይጠፋሉና፤ ሕግም ሳላቸው ኃጢአት ያደረጉ ሁሉ በሕግ ይፈረድባቸዋል፤

፤ በእግዚአብሔር ፊት ሕግን የሚያደርጉት ይጸድቃሉ እንጂ ሕግን የሚሰሙ ጻድቃን አይደሉምና።

፤ ሕግ የሌላቸው አሕዛብ ከባሕርያቸው የሕግን ትእዛዝ ሲያደርጉ፥ እነዚያ ሕግ ባይኖራቸው እንኳ ለራሳቸው ሕግ ናቸውና፤

፤ እነርሱም ሕሊናቸው ሲመሰክርላቸው፥ አሳባቸውም እርስ በርሳቸው ሲካሰስ ወይም ሲያመካኝ በልባቸው የተጻፈውን የሕግ ሥራ ያሳያሉ። (ወደ ሮሜ ሰዎች ምዕ. 2÷11-15)

+ይኽ ሕገ ልቦና የተባለው ያን ጊዜ በተፈጥሮ እንደተሰጠ ያለ የጸናም ሕግ ይሁን እንጂ የሰው ልጅ በሕገ ልቦና ብቻ ሊጠበቅ ባለመቻሉ በግድ የጹሑፍ ሕግ አስፈለገ። ስለዚህም እግዚአብሔር አምላክ በእጁ ጽፎ ሌላ ሕግን በሙሴ አማካይነት ለጊዜው ለእሥራኤል ወገን ፍጻሜው ግን ለሰው ልጅ ሁሉ ሰጥቷል። ቀጥሎም የጌታ ደቀ መዛሙርት ሐዲሱን የኪዳን ሕግ (ስድስቱን ቃላት ወንጌል) በጹሑፍ አበርክተዋል።

++++++++++

።።2።። አሠርቱ ቃላት: አሠርቱ ትዕዛዛት: አሠርቱ ሕግጋት: ሕገ መጽሐፍ(ሕገ ኦሪት):-

የሚባሉት እግዚአብሔር አምላክ ግንኙነቱን ከእስራኤል ህዝብ ጋር በማድረግ መገናኛ ይሆኑ ዘንድ የሠራቸውና የደነገጋቸው ሲሆኑ: በእግዚአብሔር ጣቶች የተጻፉ አሠርቱ ቃላት እየተባሉ የሚጠሩ ናቸው። እነዚህም እግዚአብሔር በሁለት ሠሌዳ ጽፎ ለእስራኤል ያስተላለፈው ሕግ ነው።

ሁለቱ የሕግ ጽላት የአስርቱ ቃላት ማደሪያ ሠሌዳ ሁነው የተሰጡ ናቸው። እንደ ሊቃውንቱ አስተያየት በአንደኛው ጽላት ሦስት ቃላት እግዚአብሔር ወይም እግዚአብሔር አምላክን የሚመለከቱ ለእርሱ ልናደርግና ልንፈፅመው የሚገባንን የሚገልጡ ናቸው። በሁለተኛው ጽላት ደግሞ ሰባት አንቀጾች ተጽፈውበታል: ይኸውም ሰውን የሚመለከቱ ማለት ሰው አንዱ ለሌላው ሊያደርገውና ሊፈጽመው የሚገባውን የሚያሳዩ አሠርቱ ቃላት በመጀመሪያ ለሰው መመሪያ እንዲሆኑ በጽሁፍ የተላለፉ ህግጋት ናቸው። ምክንያቱም የሰው ልጅ በመጀመሪያ በሕገ ልቦና እንዲሁም በሕገ ህሊና በሕግ ሊጸና ለእግዚአብሔርም ሊታዘዝ ተፈጥሮ ነበር: ይህ ግን ባለመቻሉ በጧትና በማታ እያነበበ: እያየም ሰው የሆነ ሁሉ እንዲጠብቀውና እንዲፈጽመው እግዚአብሔር አምላክ ስለፈቃደ ሕጉን በጽሁፍ ሰጠው እነዚህ በጽሁፍ የተላለፉ የብሉይ ኪዳን ሕግጋት ለክርስቲያኑ ህዝብ አሁንም አስፈላጊዎች ናቸው።

+ ከአሠርቱ ቃላት ዘጠኙ ተጠብቀው አንደኛው እንኳን ከፈረሠ አሠርቱ ሕግጋት ሁሉ እንደፈረሱ ይገመታል እንጂ የዘጠኙ መጠበቅ ምንም ዋጋ የለውም። ለምሳሌ አሥር በር ያለው ቤት ቢኖር ዘጠኙ በሮች ቢዘጉና አንዱ ክፍቱን ቢያድር: ሌባ ክፍት በሆነው በአንደኛው በር ገብቶ ንብረቱን ሁሉ ከወሰደው የዘጠኙ በሮች መዘጋት ምንም ጥቅም አላስገኘም ማለት ነው የአንደኛው መከፈት ለንብረቱ መጥፋት ምክንያት ሆኗልና። አሠርቱ ቃላትም በትክክል ካልተጠበቁ ዋጋ የማያሰጡ መሆናቸውን ሐዋርያው ያዕቆብ እንዲህ ሲል ያስረዳል:-

” ሕግን ሁሉ የሚጠብቅ፥ ነገር ግን በአንዱ የሚሰናከል ማንም ቢኖር በሁሉ በደለኛ ይሆናል፤ አታመንዝር ያለው ደግሞ። አትግደል ብሎአልና፤”

(የያዕቆብ መልእክት 2:10)

=======(10ቱ ትእዛዛት) አሥርቱ ትዕዛዛት==========

ከእግዚአብሔር አምላክ በቀጥታ በሙሴ አማካኝነት ለእስራኤላውያን የተሰጠ ሕግ ነው፡፡ የተሰጡትም እስራኤላውያን ከግብጽ ከወጡ በ3ኛው ወር ፋሲካን ካከበሩ በ3ኛው ቀን በደብረ ሲና ሰፍረው ሳለ ነበር፡፡ ዘፀ. 19፡1-4 በዘዳ. 34፡28 ዘዳ. 4፡13 ላይ አሥሩ ትዕዛዛት አሥር መሆናቸውን እንረዳለን፡፡

በዝርዝር ተጽፈው የሚገኙት ግን በዘዳ. 20፡ 3 እና17 እና ዘዳ. 5፡5-21 ላይ ነው፡፡ አሥርቱ ቃላትና ስድስቱ ቃላተ ወንጌል ለእስራኤል ዘስጋና ለእስራኤል ዘነፍስ የተዘጋጁ ስለሆነ ሁላችንንም ይመለከታል፡፡ እነርሱም፡-

  1. ‹‹ እግዚአብሔር አምላክህ እኔ ነኝ፡፡ ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ የማናቸውንም ምሳሌ የተቀረጸውን ምስል ለአንተ አታድርግ፤ አትስገድላቸው፤ አታምልካቸው ›› ዘፀ. 20፡2-6

  2. ‹‹ የእግዚአብሔር የአምላክን ስም በከንቱ አትጥራ፡፡ ›› ዘፀ. 20፡7

  3. ‹‹ የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ /አክብረውም/ ›› ዘፀ. 20፡ 8

  4. ‹‹ አባትህንና እናትህን አክብር ›› ዘዳ. 20፡12

  5. ‹‹ አትግደል ›› ዘፀ. 20፡13

  6. ‹‹ አታመንዝር ›› ዘፀ. 20፡14

  7. ‹‹ አትስረቅ ›› ዘፀ. 20፡15

  8. ‹‹ በሐሰት አትመስክር ›› ዘፀ. 20፡16

  9. ‹‹ የባልንጀራህን ንብረት አትመኝ ›› ዘፀ. 20፡17

  10. ‹‹ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ ›› ዘሌ. 19፡18

– አሥርቱ ሕግጋት የብሉይ ኪዳን መሠረቶች ናቸው፡፡ የእግዚአብሔርን ሕግ ብትጠብቁ ብትፈጽሙትም ሕዝቤ ትሆናላችሁ እኔም አምላክ እሆናችኋለሁ ብሎ ቃልኪዳን ገባ፡፡ ሕዝቡም በአንድ አፍ ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ‹‹እግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እናደርጋለን እንታዘዛለን›› ብለው ቃል ኪዳን ገቡ፡፡ ዘፀ. 19፡8፤ 24፡1-8 ቅዱስ ጳውሎስም እንደነገረን ይህ ፊተኛው ኪዳን ያለ ደም አልተመረቀምና ዕብ. 18፡ 22 ሙሴ ኪዳኑን ለማጽናት የደም መርጨትን ሥርዓት እንዳደረገ በሐዲስ ኪዳንም ቢሆን ሥነ ሥርዐቱ ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት ያላቸው ሕግጋት ናቸው፡፡ ማቴ 5፡17፣ 19፡15-22 ፣ዮሐ1፡12 እግዚአብሔር ሕዝቦቹና ልጆቹ ሊያረገን ይህን ታላቅ ተስፋ በመስጠት ቃል ከገባልን እኛ ደግሞ ትዕዛዙን ለመጠበቅ ምን ያህል ቃል ገብተንለታል? ጌታችን ብትወዱኝስ ትዕዛዜን ጠብቁ ዮሐ 14፡15 እንዲሁም ከሆነ እንደ እስራኤላውያን እግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እናደርጋለን እንታዘዛለን ብለን ከሁሉ በፊት ለእግዚአብሔር ቃል መግባት አለብን፡፡ ክርስትናውን ስንጀምር የመጀመርያ ሥራችን መሆን ያለበት ይህ ነው፡፡

የዐሥርቱ ትዕዛዛት ዓላማ

ዐሥርቱ ትዕዛዛት የተሰጡት በሚከተሉት ዓላማዎች ነው፡፡ ይኸውም፡-

  1. ከግብጽ ምድር ስላወጣቸው ውለታውን እንዲያስቡ

  2. ወደ ፊት በአረማዊያን መካከል ሲመላለሱ ከኃጢአት እንዲቆጠቡ

  3. መንፈሳዊ አካሄዳቸው ምን ምን አቅጣጫ መከተል እንዳለበት ለማሳየት ነው፡፡

የዐሥርቱ ትዕዛዛት አከፋፈል

የክርስቲያን ሕግ የፍቅር ሕግ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ሌላውን የሚወድ ሕግን ፈጽሞበታል ካለ በኋላ ከዐሥርቱ ትዕዛዛት የተወሰኑትን በመጥቀስ ፍቅር የሕግ ሁሉ ፍጻሜ መሆኑን በግልጽ ይነግራል፡፡ ሮሜ 13፡8-10 ታዲያ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረ ፍቅር በሁለት ይከፈላል፡፡ ማቴ 22፡34-41

1 ፍቅረ እግዚአብሔር

2 ፍቅረ ቢጽ

  1. ፍቅረ እግዚአብሔር ከአንደኛ ትዕዛዝ እስከ ሦስተኛው ያሉት ሲሆኑ እግዚአብሔርን የሚመለከቱ ናቸው፡፡

  2. ፍቅረ ቢጽ ከአራተኛ ትዕዛዝ እስከ አሥረኛ ትዕዛዝ ያሉት ሲሆኑ ባለእንጀራን የሚመለከቱ ናቸው፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ በአዎንታዊና በአሉታ ከመነገራቸው አንጻር በሁለት ይከፈላሉ ይኸውም፡-

  1. ሕግ በአሉታ የተነገሩ /አታድርግ/

  2. ትዕዛዝ በአዎንታ የተነገሩ /አድርግ/

ከዚህም ሌላ ከአፈጻጸማቸው አንጻር ሲታዩ በሦስት ይከፈላሉ፡፡

  1. በሐልዮ የሚፈጸሙ 1፣3፣4 እና 9 በሐሳብ

  2. በነቢብ የሚፈጸሙ 2፣ 8 በመናገር

  3. በገቢር የሚፈጸሙ 5፣6፣7 እና 10 በሥራ ናቸው፡፡

=======6ቱ ቃላተ ወንጌል (ስድስቱ ቃላተ-ወንጌል)======

 

1/ ለተራበ ማብላት፣ ማቴ( 25÷35)

2 /የተጠማ ማጠጣት፣ ማቴ(25 ÷3)

3 / እንግዳ መቀበል፣ ማቴ( 25 ÷ 35)

4 / የታረዘ ማልበስ፣ ማቴ ( 25_ 35)

5/የታመመን ማየት፣ ማቴ( 25÷36)

6/ የታሰረ መጠየቅ፣ ማቴ(25÷36)

 

ስድስቱ ህግጋተ-ወንጌል

1/ በወንድምህ ላይ በከንቱ አትቆጣ። (ማቴ 5÷22_17

2/ ወደ ሴት አትመልከት በልብህም አታመንዝር። ( ማቴ5÷27)

3/ ሚስትህን ካለ ዝሙት ምክንያት አትፍታ። ( ማቴ 5÷32)

4/ ፈፅመህ አትማል። ማቴ (5_÷34)

5/ ክፉን በክፉ አትመልስ። (ማቴ_ 5÷39)

6 / ጠላትህን ውደድ። ማቴ(5÷45)

 

ዳውንሎድ ሞባይል አፕ

ሶሻል ሚድያ ላይ ያግኙን

 

Copyright © 2010 – 2023 zetewahedo.com | All rights reserved.
error: Content is protected !!
Scroll to Top