ነገረ ማርያም

ነገረ ማርያም

መጋቤ ሃይማኖት ቀሲስ አሐዱ አስረስ

ነገረ ማርያም ከሁለት ቃላት የተገኘ ነው። ነገር፣ የአንድን ትምህርት መግለጫ አጉልቶ የሚያሳይ ሲሆን

ማርያም፣ የእመቤታችን መጠሪያ ስም ነው።

በመሆኑም ነገረ ማርያም ማለት በእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በኩል እግዚአብሔር ወዶ ፈቅዶ ለሰው ልጅ የገለጠውን ምሥጢር የምንማርበት ትምህርት ነው። ስለ እመቤታችን ያለው ትምህርት እጅጉን ሰፊ ስለሆነ በዚች መልእክት ላይ ነገረ ማርያምን ለማስፈር አይሞከርም። አባይን በጭልፋ ቀድቶ መጨረስ እንደማይቻል ሁሉ የእመቤታችንንም ነገር አስተምሮ ለመጨረስ አይቻልም። ነገር ግን በዚህ መልእክት ሦስት አበይት ነጥቦችን እናነሳለን። እነርሱም፦

፩. የቅድስት ድንግል ማርያም የትውልድ ሐረግ

፪. የድንግል ማርያም የስሟ ትርጓሜ

፫. እመቤታችን የምትታወቅባቸው ተጨማሪ ስሞች

፩. የቅድስት ድንግል ማርያም የትውልድ ሐረግ

እግዚአብሔር አምላክ ማደሪያው ሁሉ ንጹሕና ቅዱስ ፍጹምም ነው።ስለሆነም እርሱ ያደረበት ሰውም ሆነ ቦታ ወይም ንዋይ ሁሉ ቅዱስ ይባላል። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአምላክ ማደሪያ ሆና ስለተገኘች ቅድስት ትባላለች። የተገኘችውም እግዚአብሔር ካደረባቸው ቅዱሳን ስለሆነም ጭምር ቅድስት ተብላለች።

፪. የድንግል ማርያም የስሟ ትርጓሜ

ማርያም ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ማሪሃም ከሚለው ቃል የተወሰደ ሲሆን ትርጉሙም የብዙኃን እናት ማለት ነው፤ አብርሃም

ማለት የብዙኃን አባት ማለት እንደሆነ። (ዘፍ. ፲፯፥፭) በቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት የቅድስት ድንግል ማርያምን ስም እንደሚከተለው ያመሰጥሩታል፦

ማርያም ማለት፦

ሀ. መርሕ ለመንግሥተ ሰማያት (ወደ መንግሥተ ሰማያት መርታ የምታገባ) ማለት ነው፦

የአዳም ዘር በሙሉ በኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ወደ ገነት የገባው ወይንም ወደ ቀደመ ክብሩ የተመለሰው ኢየሱስ ክርስቶስ የእርሷን ሥጋ ተዋሕዶ በመወለዱ ስለሆነ እንዲሁም ወደ ዘለዓለም ሕይወት የሚያስገባው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙም ከርሷ የነሣው በመሆኑ ነው። በተጨማሪም የድንግል ማርያምን አማላጅነት ሳያምኑ መንግሥተ ሰማያት መግባት አይቻልምና ነው።

ለ. ጸጋና ሐብት ማለት ነው፦

የእመቤታችን ወላጆች ለጊዜው በመምከናቸው በሰው ዘንድ ተንቀው የነበሩ ሲሆን የእርሷ መወለድ ሀብት እና ጸጋ ሆኗቸዋል። ፍጻሜው ግን አማላጅነቷን ዐውቀው ቃል ኪዳኗን አምነው ለሚመጡ ምእመናን ሁሉ ሀብት እና ጸጋ ሆና ተሰጥታለች። (ዮሐ ፲፱፣ ፳፯) በበደሉ ምክንያት ከጸጋ እግዚአብሔር ተራቁቶ በእግረ አጋንንት ይቀጠቀጥ የነበረው አዳም ጸጋው ተመልሶለት ሀብተ መንፈስ ቅዱስን ገንዘብ ያደረገው በእመቤታችን በኩል ነው። “አዳም ከገነት በተባረረ ጊዜ ተስፋው አንቺ ነሽ” ብሎ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው ያመሰገናትም ለዚህ ነው።

ሐ. በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ፍጽምት ማለት ነው፦

እግዚአብሔር በባሕርዩ ፍጹም አምላክ ስለሆነ ለምሥጢረ ሥጋዌ ሰው ይሆንባት ዘንድ በመለኮታዊ ጥበቡ የመረጣት በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ ፍጽምት ትሆን ዘንድ ይገባልና በሥጋም በነፍስም ፍጽምት አደረጋት።

መ. ከፍጡራን በላይ ከፈጣሪ በታች ማለት ነው፦

እግዚአብሔር በፈጠራቸው በመላእክትና በቅዱሳን ላይ በረድኤት ወይንም በጸጋ ነው ያደረባቸው። በድንግል ማርያም ላይ ግን በረድኤትና በጸጋ ብቻ ሳይሆን ከሥጋዋ ሥጋን፤ ከደሟ ደምን፤ ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ ነው የተገለጠው(ሰው የሆነው)። ለዚህም ነው መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል “አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ” ያላት (ሉቃ ፩፣፳፰)። ስለሆነም ድንግል ማርያም ከመላእክትም ከቅዱሳንም ትበልጣለችና ከፈጣሪ በታች ከፍጡራን በላይ ተብላለች።

ሠ. የብዙዎች እናት ማለት ነው፦

አንድ ቤት የቤት እመቤትና አባወራ እንዳለው ሁሉ በክርስቶስ አምነው ላሉ ክርስቲያኖች ሁሉ እመቤታቸው (እናታቸው) ድንግል ማርያም ናት፤ የቤታቸው ራስ ልጇ አማኑኤል እንደሆነ ማለት ነው።

ረ. በእግዚአብሔርና በሰው መካከል የምትላላክ ማለት ነው፦

ለሰዎች በሥጋ ዘመዳችን ስትሆን ለፈጣሪ ደግሞ እናቱ ነች፤ በመካከል ሆና የምታገናኘን ወይንም የምታማልደን ስለሆነች በሰውና በፈጣሪ መካከል ያለች መካከለኛ ትባላለች። የሰውን ልመና ወደ እግዚአብሔር፣ የእግዚአብሔርንም ይቅርታ ወደ ሰው በማድረስ ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስ፣ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ እያማለደች ታሰጣለችና።

፫. እመቤታችን የምትታወቅባቸው ተጨማሪ ስሞች

  • እመ አምላክ   

  •  ወላዲተ አምላክ    

  • ኪዳነ ምሕረት

  •  እምነጽዮን   

  •  ሰአሊተ ምሕረት

  • ሶልያና       

  • አዶናዊት 

  •  ቤዛዊተ ዓለም

መጋቤ ሃይማኖት ቀሲስ አሐዱ አስረስ

ኦ ብእሲቶ – አንቺ ሴት

ሴት የሚለው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ የተሰጠው ቦታ እጅግ ከፍ ያለ ነው፡፡ ቃሉን ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀመበት አባታችን አዳም ነው፡፡ እግዚአብሔር ከ አዳም ግራ ጎን አንዲት አጥንት ወስዶ እጅግ ውብ እና ድንቅ የሆነች ሔዋንን ፈጥሮ ቢሰጠው በተደምሞ “ይህች አጥንት ከአጥንቴ ናት፥ ሥጋም ከሥጋዬ ናት እርስዋ ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል።” ሲል ጠራት፡፡ ዘፍ ፪፥፳፫። ሴት የሚለውን መጥሪያ አዳም የሰጠበት ዋናው ወይንም ዐቢይ ምክንያት ምን እንደሆነ እዚሁ ተገልጦልናል፡፡

እርሱም “አጥንቷ ከአጥንቴ ሥጋዋም ከሥጋዬ” ስለሆነ የሚለው ነው፡፡ የቃሉ ጥንት ከመነሻው ይኽን ይመስላል፡፡ ከቃሉ አብነት የምንረዳው የሰው ሁሉ አባት አዳም እጅግ አቅርቦ የራሱ እንደሆነች ሲያመለክት ቃሉን እንደተጠቀመበት ነው፡፡ ለዚህ አባባል ማጠናከሪያ የሚሆነን ሦስተኛ ወንድ ልጁን ለአቤል ምትክ የሚሆን ተሰጠኝ ሲል “ሴት” ብሎ መሰየሙ ነው፡፡ “ልጅንም በምሳሌው እንደ መልኩ ወለደ ስሙንም ሴት ብሎ ጠራው።” እንዲል፡፡ ዘፍ ፭፥፫። እርሱን ከመምሰል ጋር እንዴት እንዳያያዘው ስንረዳ ቃሉ የማቅረብ እንደሆነ ያስገነዝባል፡፡ በምሳሌው እንደ መልኩ መወለዱ ሴት የሚለውን ስያሜ ከአባቱ እንዲያገኝ በአመክንዮነት ሰለቀረበ በዚህ እንረዳለን፡፡

በእርግጥ ከእመቤታችን ውጪ ሌሎች ሴቶችን ጌታችን በዚህ አጠራር አልጠራም ማለት አይደለም፡፡ ለምሳሌ ከነናዊቷን ሴት፣ ስታመነዝር የተገኘቸውን ሴት እና መግደላዊት ማርያምን በመቃብሩ ስፍራ በተመሳሳይ እንደጠራቸው እንረዳለን፡፡ ታዲያ ይህ ከሆነ ለእመቤታችን ሲሆን እንዴት የተለየ ነው ልንል እንችላለን? ሚል ጥያቄ ሊነሣ ይችላል፡፡ አንድ ልጅ የወለደችውን እናቱን “እማማ” እንደሚላት ሁሉ በእናቱ ዕድሜ እንዳሉ ያሰባቸውን ሌሎች እናቶችንም “እማማ” ብሎ ሊጠራቸው ይችላል፡፡ ይህ ማለት ግን ሁሉም በሥጋ እናቶቹ ናቸው ማለት እንዳልሆነው ሁሉ ጌታችን

እመቤታችንን በዚህ ሲጠራት እና ሌሎችን ሲጠራም እንዲሁ ይለያያል፡፡
ዳግማዊ አዳም ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም በመጣ ጊዜ መጻሕፍት እንዳስረዱን “አንቺ ሴት” የሚለውን ቃል ለእመቤታችን ሁለት ጊዜ ተናግሮታል፡፡ የመጀመሪው ጌታችን በቃና ዘገሊላ በቤተ ዶኪማስ በጉባኤ በአደባባይ ሰው ሁሉ እየሰማው የተናገረው ነው፡፡ ይኽም እመቤታችን የወይን ጠጅ ማለቁን ማንም ሳይነግራት በተሰጣት ሀብት ዐውቃ (ምልዕተ ጸጋ ናትና) “የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” ባለችው ጊዜ ተገቢውን መልስ ሲመልስላት ነው፡፡ ያን ጊዜ “አንቺ ሴት” ሲል እናቱን ጠራት፡፡ ዮሐ ፪፥፬። እንግዲህ ምን ማለቱ ይሆን?
ሌላ ጥያቄ እንዳናነሣ እርሱ ቅሉ ሐጋጌ ሕግጋት (ሕግጋትን ደንጋጊ) የባሕርዪ አምላክ በመሆኑ “አባትህን እና እናትህን አክብር” ብሎ ቅድመ ሥጋዌ (ቅድመ ተዋሕዶ ወይንም ሰው ከመሆኑ በፊት) ያዘዘ ነውና እናቱን ክብር ነፈጋት ማለት ይሆንብናል፡፡ ማክበሩንማ እናውቅ ዘንድ “ከእነርሱም ጋር ወርዶ ወደ ናዝሬት መጣ፥ ይታዘዝላቸውም ነበር።” ብሎ መጽሐፍ ነገረን፡፡ ሉቃ ፪፥፶፩፡፡ እርሱን በዚህ መጠርጠር እርሱን አለማመን ይሆንብናል፡፡ እኛ ደግሞ አምላከ አማልክት፣ እግዚእ ወአጋእዝት፣ ንጉሠ ነገሥታት፣ አልፋ ወ ዖሜጋ፣ ብለን እናምነዋለን እናመልከዋለንም፡፡ ራእይ ፲፯፥፲፬፣ ፲፱፥፲፮ ፤ ፩ ጢሞ ፮፥፲፭፡፡

ቃል ሥጋን የተዋሐደው ከሰማይ አምጥቶ አይደለም፡፡ ቢያደርግ የሚቸግረው ሆኖ ሳይሆን ፍጹም ሰው ለመሆን የአዳምን ሥጋ መዋሐድ የግድ ስለሆነ ነው፡፡ ዳግማዊ አዳም የተባለውም በአማን የእኛን ሥጋ ስለተዋሐደ ነው፡፡ ፩ ቆሮ ፲፭፥ ፵፭። የዳዊት ልጅ ለመባልም አልገደደውም፡፡ ዘመን የማይቆጠርለት መለኮት በዚህ ጊዜ ነበረ በዚህ ጊዜ አልነበረም የማይባለው ቃል ለተዋሕዶ የመረጠው የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥጋ ነው፡፡ እርሷን በንጽሕና አጊጣ እና ተሸልማ ቢያገኛት ለተዋሕዶ መረጣት፡፡ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ ሰው ሆነ፡፡ ስለዚህም አንቺ ሴት አላት፡፡

ቀዳማዊው አዳም ይህች አጥንት ከአጥንቴ ሥጋዋም ከሥጋዬ ሲል ሴት እንዳላት ሁሉ ዳግማዊው አዳም ደግሞ ከሰማይ ሥጋ አላመጣሁም ሥጋዬ ከሥጋሽ አጥንቴም ከአጥንትሽ ሲል “አንቺ ሴት” ብሎ እናቱን ቅድስት ድንግል ማርያምን በወግ በማዕረግ ጠራት፡፡ ይህ አጠራር ድንቅ ነው! ይህ አጠራር በአማን ልዩ ነው! መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማክበሩን ብቻ ሳይሆን የመታዘዙን ወሠን እስኪ እንመልከተው፡፡ ለዚህ ትኅትናውስ ምን ቃል እናገኝለታለን!

ጌታችን አንቺ ሴት ማለቱ ሰው በተሰበሰበበት በአደባባይ እናትነቷን ማረጋገጡ ነው፡፡ ሌሎች እናቶች እናትነታቸው በአባት የታጀበ ነው፡፡ የእርሷ እናትነት ግን ያለ አባት እንበለ ዘርዐ ብእሲ ነው፡፡ የልዩነቱን ርቀት እስኪ እንለካው፡፡ ይህ በኅሊናችን ዘወትር ተስሎ ይኖር ዘንድ “አንቺ ሴት” ብሎ ጠራት፡፡ በሌላ አጠራር ለመጥራት ገድዶት አይደለም፡፡ ይኽኛውን ወድዶት እንጂ፡፡ “ኩሎ ዘፈቀደ ገብረ እግዚአብሔር በሰማይኒ ወበምድር በባሕርኒ ወበቀላያት – በሰማይም በምድርም በባሕርም በጥልቆችም እግዚአብሔር የወደደውን ሁሉ አደረገ” እንዲል የወደደውን ለማድረግ ማን ከልካይ አለበት? መዝ ፻፴፬፥፮።
ይህን አጠራር በተለየ ጌታችን ወድዶታል ለማለት እንችላለን ወይ? ብንል እርሱ ራሱ እመቤታችንን በድጋሚ በዚሁ አጠራር መጥራቱ ያረጋግጥልናልና መልሳችን አዎ ብቻ ነው፡፡ እርሱም በቀራንዮ በመስቀል ላይ ሆኖ በጠራት ጊዜ ነው፡፡ “አንቺ ሴት እነሆ ልጅሽ” ያለበት ድምጽ ልዩ ቃና ያለበት ነው፡፡ ዮሐ ፲፱፥፳፮።
ሁለቱም ሁኔታዎች በተመሳሳይ ያስተላለፉት ዐቢይ መልእክት አለ፡፡ የእመቤታችንን ክብር! ምክንያቱም፡- በአደባባይ መናገሩ ነው፡፡ ጌታችን በሁለቱም ጊዜያት እመቤታችንን “አንቺ ሴት” ያለው በጣይ በጉባይ ነው፡፡ በቃናው ሠርግም እድምተኞች ነበሩ፣ በቀራንዮ አደባባይም እንዲሁ ሰዎች ነበሩ፡፡ የእመቤታችን እናትነት እንዲህ በአደባባይ መነገሩ ሁሉም በሚገባ ያውቀው ዘንድ የተደረገ ታላቅ ዐዋጅ ነው፡፡ እመቤታችን እንዲህ ከፍ ባለ መድረክ በሚሰማ ድምጽ የተሰጠችን እንጂ ናት፡፡

እስኪ እናስተውል ጌታችን በተለይ በዚያች የጭንቅ ጭንቅ ሰዓት በተደራረበ መከራ መስቀል ውስጥ ሆኖ ይህን ቃል እንደምን ተናገረው? ሁኔታው የማይታለፍ ደረጃው ከፍ ያለ መሆኑን የምናየው ከተናገራቸው ጥቂት ንግግሮች መሀል የእናቱን ነገር በመጨመሩ ነው፡፡ ከሰባቱ አጽርሐ መስቀል አንዱ “አንቺ ሴት” የሚለው ነውና፡፡ የቃላቱ ጥቂት መሆን፣ የሰዓቲቱ አስጨናቂ መሆን፣ የእርሱ እጅግ በደከመ ጊዜም ቢሆን ከፍ ባለ ድምጽ መናገር ለጉዳዩ ልዩ ትኩረት እንድንሰጥ ያስገድደናል፡፡ እናቱን መቼም ቢሆን ሊተዋት እንደማይችል ከዚህ በላይ እንዴት ይገለጣል፡፡ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ያነጋገረችው እርሷ ናት፡፡ የመጣበትንም የቤዛነት ሥራ ፈጽሞ ወደ ቀደመ መንበሩ ወደ የማነ አብ ዘባነ ኪሩብ ሲሄድም የተነጋገረው ከእርሷ ጋር ነው፡፡
ስለሆነም እመቤታችን ራሷ ምሥጢር ናት፡፡ መጠሪያዋ እንደ አሸዋ የበዛው እንዲሁ እንዳልሆነ የማያውቅ ክርስቲያን መኖር የለበትም እና ስለእርሷ ተናግሮ መድከም አይኖርም፡፡ ጌታችንም በሕማም በደከመ ጊዜ እንኳ ስለ እርሷ ነግሮናልና፡፡

ይኽንን እናውቅ ዘንድ የረዳን አምላካችን እግዚአብሔር ይመስገን፡፡

ኪዳነ ምሕረት

✍ በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ

❖ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ “ቃል ኪዳን” የሚለው ቃል 257 ጊዜ በላይ ተጠቅሷል፤ ኪዳን ማለት ቃል “ተካየደ” ከሚለው ከግእዝ ቃል የወጣ ሲኾን “ተዋዋለ፣ ተስማማ፣ ተማማለ” ማለትን ሲያሳይ እግዚአብሔር ሰውን ከማፍቀሩ የተነሣ ለሰው ልጅ እንደ ባልንጀራ አድርጎ መሐላን ይምላል፣ ቃል ኪዳንም ይገባል፡፡

❖ ክቡር ዳዊት በመዝ 88፡2-3 ላይ “ከመረጥኋቸው ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ” እንዳለ ከኹሉም ቅዱሳን በላይ ኾና ሰማይ ምድር የማይወስኑትን አምላክ በማሕፀኗ ለመሸከም፣ ኪሩቤል ሱራፌል ዙፋኑን በመፍራትና በመንቀጥቀጥ የሚሸከሙትን ሰማያዊ መለኮትን በዠርባዋ ለማዘል፣ በክንዷ ለመታቀፍ፣ ሰማይ ምድር ከፊቱ የሚሸሹትን የባሕርይ አምላክን በከናፍሮቿ ለመሳም፣ ፍጥረታትን ኹሉ በዝናብ አብቅሎ በፀሓይ አብስሎ የሚመግበውን፤ ለቅዱሳን መላእክት ርሱ የገለጸላቸው ምስጋና ምግብ ኹኗቸው እንዲኖሩ ያደረገውን ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የተካከለውን እግዚአብሔር ወልድን የድንግልና ጡቶቿን ለማጥባት ከተመረጠች ከእናቱ ጋር የገባው ጽኑዕ የምሕረት ቃል ኪዳን እጅግ ልዩ እና ለኃጥኣን ኹሉ ተስፋ የሚኾን ነው፡፡

❖ መልአከ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤልም በአምላክ እናት ፊት ቆሞ “ማርያም ሆይ በእግዚአብሔር ፊት ሞገስን አግኝተሻልና አትፍሪ” በማለት ከፍጡራን ወገን ማንም ሊያገኘው የማይችለውን ይኸውም በልዑል እግዚአብሔር ዘንድ መወደድን በማግኘት ከባለሟልነት ኹሉ የላቀ ባለሟልነት ይኸውም የአምላክ እናት የመኾንን የማማለድ ልዩ ጸጋና ክብር እንደተሰጣት ነግሯታል፡፡

❖ መልአኩ በዚኽ ምስጋናው ላይ “ሞገስን አግኝተሻልና” አለ እንጂ “ወደ ፊት ታገኛለሽ” አለማለቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ጥንቱኑ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ የተጠበቀችና በልዑል የተመረጠች መኾኗን የሚያረጋግጥም ነበር፡፡ ከዚኽ ከተሰጣት ታላቅ ባለሟልነት የተነሣ ልጇን በማሳሳብ ውሃው ወደ ወይን እንዲለወጥ አስደርጋለች (ዮሐ 2፡1-10)፡፡

❖ በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ውስጥ እንደምናነብበው በአምላካቸው ፊት ባለሟልነትን ያገኙ ብዙዎች ቅዱሳን ቢኖሩም ቅሉ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ግን ለነዚኽ ኹሉ ቅዱሳን ሰማያዊ ክብርን ቃል ኪዳንን የሰጠውን አምላክን በድንግልና ፀንሳ በድንግልና በመውለዷ “ወላዲተ አምላክ” የመባል ታላቅና ልዩ ባለሟልነት ተሰጥቷታልና የርሷ ክብር ከማንም ቅዱሳን ክብር ጋር ፈጽሞ የማይነጻጸር ነው፡፡

❖ ከ 432-447 ዓ.ም ሴሌኡሲያ ላይ ጳጳስ የነበረው ሊቁ ባስልዮስም እግዚአብሔር ለእናቱ የሰጣት ልዩ ባለሟልነትን ከቅዱሳን ጋር በማነጻጸር ሲጽፍ “What encomiums can we offer her as she deserves, when everything of this world is beneath her merits?…” (የሚመጥናትን ምን ዐይነት ልዩ ምስጋና እናቅርብላት? የዚኽ ዓለም ነገር ኹሉ አይመጥናትምና፤ ቅዱስ ጳውሎስ ስለ ቅዱሳን ሲናገር “ዓለም አልተገባቸውም” (ዕብ ፲፩፥፴፰) ካላቸው፤ ለአምላክ እናትማ ከከዋክብት በላይ ኾና እንደምታበራው ፀሓይ ለኾነችው ለርሷ ምን ልንል እንችል ይኾን? (ራእ ፲፪፥፩)… ምን ምስጢር እንደተከናወነ ተመልከት፤ ኅሊናንና አእምሮን የሚያልፍ ነገር እንደኾነ አስተውል፤ ታዲያ የአምላክን እናት ታላቅነት ኹሉም ሰው እንደምን አይናገር? ማንስ ነው ከቅዱሳን ኹሉ በላይ እንደኾነች ያላስተዋለ? እግዚአብሔር ላገልጋዮቹ የሚልቅ ጸጋን ከሰጠና የሚነኩት ኹሉ ሰው ከበሽታው ከተፈወሰ፤ ጥላቸው ያረፈበት ተአምር ከተፈጸመለት፤ ጴጥሮስ በጥላው ካደነ (የሐዋ ፭፥፲፭)፤ የጳውሎስ የልብሱ ጨርቅ ዕራፊ መናፍስትን ካወጣ (የሐዋ ፲፱፥፲፩)፤ ለእናቱማ ምን ዐይነት ሥልጣንና ኀይል ተሰጥቷት ይኾን?

✔ ለቅዱሳኑ ይኽነን ያኽል ድንቅ እንዲያደርጉ ባለሟልነትን ከሰጣቸው ወልዳ ላሰደገችው እናቱማ ምን ያኽል ይሰጣት ይኾን? በምን ዐይነትስ ስጦታ አስጊጧት ይኾን? ጴጥሮስ “ክርስቶስ አንተ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ነኽ” ስላለው ብፁዕ ከተባለና የመንግሥተ ሰማያት ቊልፍ ከተሰጠው (ማቴ ፲፮፥፲፮-፲፱)፤ ርሷ ከኹሉም ይልቅ እንዴት የተባረከች (ብፅዕት) አትኾን? (ሉቃ ፩፥፵፭)፤ ጳውሎስ ታላቅ ክብር ያለውን የክርስቶስን ስም በመሸከሙ “ምርጥ ዕቃ” ከተባለ (የሐዋ ፱፥፲፭)፤ የአምላክ እናትማ የምእመናን ምግብ የኾነ መናውን ሳይኾን የሕይወት ሰማያዊ እንጀራን ያስገኘች ርሷ ምን ዐይነት ልዩ ዕቃው ትኾን?

✔ ነገር ግን ስለርሷ ብዙ እናገራለኊ ብዬ ስለክብሯ ጥቂት በመናገር ራሴን በኀፍረት ውስጥ እንዳልጨምር እፈራለኊ ስለዚኽ ካኹን ወዲኽ የንግግሬን መልሕቅ ስቤ በዝምታ ወደቤ ላይ ማረፍን መርጬአለኊ) በማለት በእግዚአብሔር ፊት የተሰጣት ባለሟልነት ፍጹም እንደኾነና ከቃላት በላይ እንደኾነ አስተምሯል፡፡

❖ ዳግመኛም ቅዱሳን መላእክትና ጻድቃን ካገኙት ሞገስ የተነሣ ወደ ፈጣሪያቸው እንዲያማልዱን ስንማጸናቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ግን የአምላክ እናት ናትና ካገኘችው ከዚኽ ታላቅ ባለሟልነት የተነሣ ወደተወደደው ልጇ እንድታማልደን እንማጸናታለን፤ ከዚኽም የተነሣ ነው ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬምም በእሑድ ውዳሴ ማርያም ላይ፦
✍ “ለኪ ይደሉ ዘእምኲሎሙ ቅዱሳን ትሰአሊ ለነ ኦ ምልእተ ጸጋ…” (ጸጋን የተመላሽ ሆይ ከቅዱሳን ኹሉ ይልቅ ትለምኚልን ዘንድ ላንቺ ይገባል፤ አንቺ ከሊቃነ ጳጳሳት ትበልጪያለሽ፤ ከነቢያትም ከመምህራንም ትከብሪያለሽ ከሱራፌልና ከኪሩቤል ግርማ የሚበልጥ የመወደድ ግርማ አለሽ፤ በእውነቱ የባሕርያችን መመኪያ አንቺ ነሽ) በማለት ያመሰገናት፡፡

❖ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም ካገኘችው ታላቅ ባለሟልነት የተነሣ ፭ሺሕከ፭፻ ዘመን ሲፈጸም ያለ ዘርዐ ብእሲ አካላዊ ቃል ክርስቶስን በኅቱም ድንግልና የፀነሰች፤ ፱ወር ከ፭ ቀን በማሕፀኗ የተሸከመች፣ በኅቱም ድንግልና የወለደች፣ በክንዷ የታቀፈች፣ በጀርባዋ ያዘለች ርሷ ብቻ ናትና፤ በርሷ አማላጅነት የምናቀርበው ጸሎት ምን ያኽል ታላቅ እንደኾነ በሰዓታት መጽሐፉ ላይ፡-

✍“ወፈድፋደሰ በእንተ ማርያም እምከ እንተ ይእቲ ትምክህተ ዘመድነ …” (ይልቁንም የባሕርያችን መመኪያ ስለምትኾን ስለ እናትኽ ስለ ማርያም አንተን በመፅነስና አንተን በመውለድ ዕድፍ ጒድፍ ስላላገኘው ስለ አልተለወጠ ድንግልናዋና ስለ ተሸከመኽ ማሕፀኗ፤ ስለ ታቀፉኽ ስለ ክንዶቿና፣ ስለ ዳሰሱኽ ስለ እጆቿ፤ ስለ ሳሙኽ ስለ ከንፈሮቿ ስለ አሳደጉኽ ስለ ጡቶቿ፤ ከአንተ ጋር ስለ ተመላለሱ ስለ እግሮቿና፤ ስለ ዐዘለኽ ስለ ጀርባዋ፤ ብሩሃት ስለሚኾኑ ስለ ዐይኖቿ በጎ መዐዛ ስላላቸው አፍንጮቿ፤ ጸዐዶች ስለሚኾኑ ጥርሶቿ፤ በመልአኩ በገብርኤል ቃል ስለ ተበሠሩ (ብሥራትን ስለ ሰሙ) ስለ ጆሮቿ፤ ከርሷ ስለነሣኸው ሥሮችና ጸጒር፣ ደምና፣ ዐፅም ስለ ነፍስና ሥጋ፤ አባቶቻችን እንደ አስተማሩን ፈጽሞ ያለመለየትና ያለመለወጥ ከመለኮትነትኽ ጋራ አንድ ያደረግኸው) በማለት እንዳስተማረ፤ በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ ባለሟልነት እንዳገኘች በብርሃናዊዉ መልአክ የተመሰከረላት የአምላካችን እናት ቅድስት ድንግል ማርያምን ከልጇ ታማልደን ዘንድ “ሰአሊ ለነ ቅድስት” (ቅድስት ሆይ ለምኝልን) እያልን እንማጸናታለን፡፡

❖ ይኸውም ታላቁ የነገረ ማርያም መጽሐፍ እንደሚያስረዳን ጌታችን ካረገ በኋላ እመቤታችን ጌታችን ወደ ተቀበረበት ጎልጎታ እየኼደች ትጸልይ ነበር፤ ከዕለታት ባንዳቸው በየካቲት ፲፮ ዕለት ስትጸልይ “አዕረግዋ ውስተ ሰማይ ከመ ያርእይዋ መካነ ዕረፍቶሙ ለጻድቃን ኀበ ሀለዉ አብርሃም ይስሐቅ ወያዕቆብ ወተቀበልዋ ኲሎሙ ነፍሳተ አበው እለ አዕረፉ እምአዳም እስከኔሁ ወሰገዱ ላቲ እንዘ ይብሉ ስብሐት ለእግዚአብሔር ዘፈጠረ ለነ ኪያኪ ሥጋ እምሥጋነ ወዐፅመ እምዐፅምነ” ይላል መላእክት አብርሃም ይስሐቅ ያዕቆብ ያሉበትን የጻድቃን የማረፊያቸውን ቦታ ያሳዩዋት ዘንድ ወደ ገነት አሳረጓት፤ በዚያም ከአዳም ዠምሮ እስከዚያው ያረፉ ያባቶች ነፍሳት ተቀብለዋት “ከዐፅማችን አንቺን ዐጥንት ከሥጋችን አንቺን ሥጋ ለፈጠረልን ለእግዚአብሔር ምስጋና ይግባው” እያሉ የአክብሮት ስግደት ሰግደውለታል፡፡

❖ ከዚያም መላእክት የጻድቅ ሰው ነፍስ ከሥጋው ሲለይ ያለውን ፍጹም ክብርና የሚወርሰውን የገነት ርስቱን መላእክት ካሳዩዋት በኋላ፤ ኃጥኣን ነፍሳቸው ከሥጋቸው ሲለይ ያላቸውን ጭንቅ ነፍሳቸው በሲኦል የምትቀበለውን ከፍተኛ መከራ አሳዩዋት፤ “ወሶበ ተስእኖሙ አምስጦ ይቤሉ እንዘ ይኬልሑ ኦ እግዝእትነ እሙ ለመድኅን ወለተ ብርሃን ንዒ ኀቤነ ከመ ትፍትሕነ እማእሰሪሁ ለሰይጣን ወኢትኅድግነ” ይላል ለማምለጥ ባልተቻላቸውም ጊዜ “የመድኅን እናቱ የብርሃን መገኛ እመቤታችን ሆይ ከዚኽ ከዲያብሎስ ቊራኝነት ታላቅቂን ዘንድ ድረሺልን ቸል አትበዪ” እያሉ ምልጃዋን ሽተው በታላቅ ጩኸት ያለቅሱ ዠመር፡፡

❖ ያን ጊዜ ርኅርኅት የኾነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም “ወይ ሎሙ ወአሌ ሎሙ መኑ እምዜነዎሙ ለውሉደ ሰብእ ኢይምጽኡ ዝየ” (ወዮላቸው ወዮታ አለባቸው ወደዚኽ እንዳይመጡ ለሰው ልጆች ኹሉ ማን በነገራቸው) እያለች ስታለቅስ፤ መላእክትም ለርሷ “ኢትፍርሂ ኦ ማርያም እስመ እግዚአብሔር ምስሌኪ ወምስለ እለ የአምኑ ብኪ” (እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ስለኾነና ባንቺ አማላጅነት ከአመኑት ኹሉ ጋር ስለ አለ አይዞሽ) በማለት ነገሯት፡፡

❖ ርሷም “እስእለከ እግዚኦ ወአስተበቊዐከ በእንተ ኲሉ ዘየአምን ብየ ረስዮ እግዚኦ ግዑዘ እምሲኦል ተዘኪረከ ረኃበ ወጽምዐ ወኲሎ መከራ ዘረከበኒ ኀቤከ ወምስሌከ” (አቤቱ በኔ ቃል ኪዳን ስላመነ ኹሉ እማልድኻለኊ እለምንኻለኊ፤ መራቤን መጠማቴንም ካንተ ጋር በምድረ ግብጽ ያገኘኝን ረኃብና ጥም ኹሉ አስበኽ አቤቱ ወደ ሲኦል ከመውረድ ነጻ አድርገው) በማለት ወደ ልጇ ፍጹም ልመናን አቀረበች።

❖ ጌታችን ተገልጾላት “ይኩን በከመ ትቤሊ እፌጽም ለኪ ኲሎ መፍቅደኪ አኮኑ ተሰባእኩ በእንተ ዝንቱ መሐልኩ ለኪ በርእስየ ከመ ኢይሔሱ ኪዳንየ” (የለመሺዉን ኹሉ ይደረግልሽ፤ የምትፈቅጂውን ኹሉ እፈጽምልሻለኊ የለመንሺዉን ኹሉ ላደርግልሽ ሰው ኹኜአለኹና፤ መሐላዬን እንዳላፈርስ አማንየ በርእስየ ብዬ በራሴ ማልኹልሽ) ሲል ለእናቱ የማያልፍ የምሕረት ቃል ኪዳንን ገብቶ ገብቶላታልና በዓሉ “ኪዳነ ምሕረት” በመባል ይታሰባል::

❖ ሊቁ ቅዱስ ያሬድም በዝማሬው ላይ ጌታ ለእናቱ ስለገባላት ቃል ኪዳን፡-
✍ “ይቤላ ለእ ማርያም እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ተካየድኩ ምስሌኪ ኪዳነ ምሕረት ከመ አድኅን ዘተአመነኪ መሐልኩ ለኪ በርዕስየ ዘመሐልኩ አነ ለኖኅ ገብርየ ወለአብርሃም ፍቁርየ፤ ዘመሐልኩ አነ ለዳዊት ኅሩይየ ብእሲ ምእመን ዘከመ ልብየ መሐልኩ ለኪ በርዕስየ በቅዱስ ሥጋየ ወበክቡር ደምየ መሐልኩ ለኪ በርዕስየ ከመ ኢይሔሱ ማእኰትየ”
✍(ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ማርያምን እንዲኽ አላት በምልጃሽ ያመነብሽን አድን ዘንድ ካንቺ ጋራ የምሕረት ቃል ኪዳንን ተጋባኊ፤ ለአገልጋዬ ለኖኅና ለወዳጄ ለአብርሃም ቃል የገባኊ እኔ በራሴ ማልኹልሽ፤ እንደ ልቤ ለምለው ለታመነው ለዳዊት የማልኊ እኔ በራሴ ማልኹልሽ፤ በቅዱስ ሥጋዬና በክቡር ደሜ የማልኊ እኔ ምዬ እንደማልከዳ ማልኹልሽ) በማለት ጽፎታል፡፡
[በቀራንዮ ከፈጣሪያችን የተቀበልንሽ ስጦታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ ልጅሽ ይቅርታውን ያድለን ዘንድ ለምኝልን]
✍ ከመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ

 

ዳውንሎድ ሞባይል አፕ

ሶሻል ሚድያ ላይ ያግኙን

 

Copyright © 2010 – 2023 zetewahedo.com | All rights reserved.
error: Content is protected !!
Scroll to Top