ውዳሴ አምላክ ዘዘወትር
ከቁጣ የራቅህ ይቅርታህ የበዛ ጻድቅ ልበ ሰፊ መሐሪ ሆይ አከብርሃለሁ። ዕለት ዕለት ስበድል ታግሠህ ጠብቀኸኛልና፤ ንስሐ እንገባ ዘንድም ለሁላችን ሥልጣን ሰጠኸን፤ስለዚህ እናከብርህ ዘንድ ክቡር ስምህን እናመሰግን ዘንድ ታገስኸን ስለምትሠራው ሁሉ የፍጥረት ሹም ሆይ ኀዘንና ፍርሃትን ድካምንም የምታመጣበት ጊዜ አለና። በነቢያት የዘለፍክበት ጊዜም ነበርና ኋላ ግን በአንድ ልጅህ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መታየት ጐበኘኸን። ካለመኖር ወደ መኖር የፈጠርኸን አንተ ነህ አባታችንም ጌታችንም አንተ ነህ። ችጋረኛ የምሆን እኔስ ከፊትህ ልናገር አይገባኝም ከኃጥአን የሚበልጥ ኃጥእ ነኝና። ክብርት ሕግህንም ያረከስኩ ነኝና ከኃጢአቴ ትዕግሥትህን ስለ አበዛህልኝ አመስግንሃለሁ። በፈቃድህ ቸል ብለህ እስከ አሁን ያለ ፍርድ ጠበቅኸኝ። እኔ ግን ስለ በደሌ ለፍርድ የተገባሁ ነኝ ስለ ኃጢአቴም ለስቃይና ከፊትህ ለመውደቅ፤ ነገር ግን ሰውን ስለመውደድህና ስለ ትዕግሥትህ እስከ አሁን ጠበቅኸኝ። መሐሪ ጌታ ሆይ፤ ስለዚህ አመሰግንሃለሁ መጠን ለሌላት ትዕግሥትህና ለጌትነትህ የሚገባ ምስጋናን አመሰግንህ ዘንድ ሥልጣን የሌለኝ የተናቅሁ ጎስቋላም ብሆን የእኔን የባሪያህን ጎስቋላና ደካማ ልመናዬን ስማኝ። ወሰን በሌላት በፍቅርህ ብዛት እስከ ዘለዓለሙ ክብርና ምስጋና መገዛትም ለአንተ ይገባል አሜን በእውነት። ኦ እግዚእየ ኢየሱስ ክርስቶስ ዕቀብ ሕይወትየ ወሥረይ ኃጢአትየ ሊተ ለ….።
ማር ይስሐቅ ፪ኛ ምዕራፍ
ወንድሜ ሰውነትህን ዘወትር ዝለፋት ከሥጋ የምትለዪበት የምታልፊበት ጊዜ ደርሷል በላት። ባለሽበት ኋላ ጥለሽው በምትሄጂ ሥራ ዛሬ ለምን ደስ ይልሻል? እርሱን በማየት ጥቂት ዘመን ተድላ ደስታ የምታደርጊበት ኋላ ብዙ ዘመን በምታጭው የቀደመ ሥራሽን እወቂ የሠራሽው ሥራ ምንም እንደሆነ አስቢ፤ጽድቅም እንደሆነ ኃጢአትም እንደሆነ፤ ያለ ዘመንሽን ከማን ጋር ፈጸምሽው? ከጌታ ጋር ነው? ወይስ ከሰይጣን ጋር ነው? ደክመሽ የሠራሽውን የሚቀበልሽ ማን ነው? ጌታ ነው? ወይስ ሰይጣን ነው? በትሩፋትሽ ማንን ደስ አሰኘሽ? ጌታን ነው ወይስ ሰይጣንን ነው? በጊዜ ሞትሽ ሊዋሐድሽ የሚመጣው ማን ነው? በመንግሥተ ሰማይ ዐርፈሽ ትኖሪ ዘንድ በሥራሽ ደስ ያለው ማን ነው? ለማን ብለሽ ደከምሽ? ለማን ብለሽ መከራ ተቀበልሽ? ለመንግሥተ ሰማይ ብለሽ ነውን? ደስ ብሎሽ ታገኚው ዘንድ አኳኋኑስ ምንድነው? ነፍስሽ ከሥጋሽ በተለየች ጊዜ በመንግሥተ ሰማይ ይዋሐድሽ ዘንድ ገንዘብ ያደረግሽው ምንድነው
ምን ምግባር ነው? በማናቸው እርሻ ሊያውሉሽ ተቃጠሩሽ በማናቸውስ መዓርግ ተቃጠሩሽ? በባለሠላሳ ነው? በባለስልሳ ነው? ወይስ በባለመቶ ነው? ነፍስሽ ከሥጋሽ በምትለይበት ፀሐይ ዕድሜሽ በገባ ጊዜ ዋጋሽን እሰጥሻለሁ ያለሽ ማነው? ጌታ ነው? ወይስ ዲያብሎስ ነው? ነፍሴ ሆይ ሰውነትሽን መርምሪ ዕዳሽ በማናቸው ቦታ እንደሆነ እወቂ፤ መንግሥተ ሰማይም እንደሆነ ገሃነምም እነደሆነ እወቂ ለሚያርሱ ሰዎች አሞጭ እሬት የሚያፈራ እርሻሽን ያረስሽ ብትሆኝ ማለት በሚሠሩት ሰዎች ፍዳን የሚያመጣ ኃጢአትን ብትሠሪ እያዘንሽ እየተቆረቆርሽ አልቅሽ ለምኝ። ከቍርባን ከመሥዋዕት ይልቅ በሱ ምክንያት ወዶ በሰው በሚያድርበት ገንዘብ ያድርበት ዘንድ ክቡራን መላእክት ደስ በሚላቸው ደስ ይላቸው ዘንድ አንደበትሽ እየራራ ያመስግን። ግራ ቀኝ ፊትሽን በዕንባ እጠቢው መንፈስ ቅዱስ ያድርብሽ ዘንድ ከኃጢአትሽ ይለይሽ ያነጻሽ ዘንድ መጥቶ ያድርብሽ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እያለቀስሽ ለምኚልኝ የልቅሶ ዜማ ማርያምን ማርታን ጥሪያቸው ማለት አብነት አድሪጊያቸው የልቅሶ ባለቤቶች ናቸውና። ለአልዓዛር ብሎ ወደ አለቀሰ ወደ ጌታ ያዝንልሽ ዘንድ ለምኝ ራርቶ ብዙ ልቅሶን ወደሚሰጥ ጌታ ለምኝ። ምርር ብዬ ያለቀስሁት ዕንባዬን ተቀበልልኝ እያልሽ ወደ እርሱ አልቅሽ። በመልዕልተ መስቀል በተቀበልከው መከራ ከደዌ ኃጢአት አድነኝ። በመስቀል ላይ በቆሰልከው ቍስል ከቍስለ ኃጢአቴ አድነኝ ከመከራ አድነኝ። ደሜን በደምህ አንጻው ብለሽ ለምኝ። ከፍዳ ከኃጢአት የሚያድን ደምህን ከሥጋዬ ጋር አዋሕድልኝ። በመስቀል ላይ በጠጣኸው ሐሞት፤ ሰይጣን እሷን ከሚያሠራት ኃጢአት ለይተህ በሰውነቴ ጣዕም አሳድርባት። በመስቀል ላይ የተዘረጋ ሥጋህ፤ አጋንንት በምክራቸው ወደ ገሃነም ለማውረድ የሳቡት ልቡናዬን ወደ አንተ ይስቀለው ወደ ፈያታይ ዘየማን ዘንበል ባለ እራስህ አጋንንት በብረት ኃጢአት የመቱት ራሴን ከፍ ከፍ አድርገው። «እምከመ ተለዓልኩ እምድር እስሕብ ኵሎ ኀቤየ» ብለህ በማይታበል ቃልህ እንደተናገርክ። ዮሐ.፲፪፥፴፪ በመስቀል የተቸነከሩ እጆችህ ከኃጢአት ከፍ ከፍ ያድርጉኝ ርኩሳን አይሁድ ትፍ ያሉበት የጸፉት ፊትህ ኃጢአት ሠርቶ ያደፈ ሰውነቴን ፊቴን ይጠበው። በመስቀል ተሰቅለህ ሳለህ «አባ አመኃፅን ነፍስየ ውስተ እዴከ» ሉቃ.፳፫፥፵፮ ብለህ የለየሃት ነፍስህ በቸርነትህ መርታ አንተ ወደ አለህበት ታድርሰኝ። «ምነው አታዝንም?» ትለኝ እንደሆነ አንተን ለመሻት ያዘነ ልቡና የለኝምና። «ምነው ንስሓ አትገባም?» ትለኝ እንደሆነ፤ ጻድቃን ወደ ማታልፍ ርስታቸው ወደ መንግሥተ ሰማያት ተመርተው የሚደርሱበት ንስሓ ኀዘን የለኝም፤ እሊያ ንስሓ ገብተው የሠሩትን ሥራ አልሠራሁምና። ጌታዬ ሆይ ኃጢአትን የሚያስተሠርይ እንባ የለኝም የዚህን ዓለም ሥራ በማሰብ ልቦናዬ ደከመ፤ተቆርቁሮ ወደ አንተ ያለቅስ ዘንድ አይቻለውም እነሆ በኃጢአት ብዛት ልቡናዬ ተባረደ። አንተን ወዶ በሚያፈሰው እንባ ፍቅር መቃጠል አይቻለውም። የሀብታት የምስጢራት መገኛ ጌታዬ እግዚአብሔር ሆይ አንተ ግን ራርተህ ፈጽሞ መመለስን ስጠኝ። በፍጹም ልቡናዬ አንተን ለመሻት እወጣ ዘንድ ያዘነ ልቡናን ስጠኝ። ከአንተ በመራቅ ከአንተ በመለየት ተሰጥቶኝ የነበረውን ክብር አጣዋለሁ። ቸር ንጉሥ ሆይ ዛሬ ግን በለጋስነትህ ስጠኝ። ዘመን የሌለው ልደትን አካልን ዘእምአካል፣ባሕርይን ዘእምባሕርይ የወለደ አባትህ አንተን መምሰልን ያጸናብኝ፤
ያሳድርብኝ ዘንድ ከክብርህ ወገን ስጠኝ ካልኩህ አንተ ግን አትጣለኝ። ከከበረ ሕግህ ወጣሁ ከፊትህ ተለየሁ። አንተም እኔን ለመፈለግ ውጣ። «እንደገባ ይውጣ እንደወጣ ይቅር» አትበለኝ። ምእመናን ወደ አሉበት ወደ መንግሥተ ሰማይ አግባኝ። ከመንጋ በጎች ከተመረጡ ከጻድቃን ጋር እንድቆጠር አድርገኝ። ንጹሕ ልቡናን ላግኛት የሚል ንጹሕ ልብ የሚረዳት የአምላክነትህ ገንዘብ የምትሆን እህል ምስጢርህን መግበኝ ከአንተ የተገኘውን ምስጢር የማይበት በአንተ ስለአመኑ ስለሚጨነቁ የሚሰጥ ጸጋ ክብር ነው የጭንቅ ጭንቅ የሚሆን መከራውን ለሚታገሡ ልዩ ልዩ የሚሆን ሥቃይን ለሚታገሡ ሰዎች የሚሰጥ ክብር ለሁላችን ምስጢር የሚገለጽበት ክብሩን በቅተን እናገኘው ዘንድ ጸጋውን የበቃን ሆነን ያገኘን ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነት ሰውን በመውደዱ ዛሬ በአለው ዓለም በሚመጣውም ዓለም፤በማይፈጸመው ዓለም ሰውን በመውደዱ አሜን በእውነት። ኦ እግዚእየ ወአምላኪየ ኢየሱስ ክርስቶስ የምሕረት
መገኛ መዓትህ የራቀ ትዕግሥትህ የቀረበ ቸርነትህ የበዛ ዕቀብ ሕይወትየ ወሥረይ ኃጢአትየ ሊተ ለ…….።
ጸሎተ ምናሴ ፩፥፩-፲፫
አቤቱ ዓለምን ሁሉ የምትገዛ የአባቶቻችን አምላካቸው። የአብርሃምና የይስሐቅ የያዕቆብም የጻድቃን የዘራቸውም ሁሉ። ሰማይና ምድርን ከዓለሞቻቸውም ሁሉ ጋር የሠራህ። ባሕርን በቃልህ ትእዛዝ የገሠጽሃት፤ጥልቆችን የዘረጋህ የሚያስፈራውንም ያተምህ ይኸውም በምስጉን ስምህ ነው። ሁሉ ከኃይልህ ፊት የሚናወጽና የሚንቀጠቀጥ ሆይ ለምስጋናህ ከፍታ ዳርቻ የለውምና የቍጣህ መቅሠፍት በኃጥአን ላይ የሚያስፈራ ነው። ለትእዛዝህ ይቅርታ ስፍር ቍጥር የለውም፤ እግዚአብሔር ሆይ አንተ ብቻህን ከፍ ያልህ ነህና። ከቍጣ የራቅህ ይቅርታህም የበዛ መሓሪ ነህና። በሰው ልጆች በደል ላይም የምትመለስ ነህ። አሁንም የጻድቃን አምላክ ሆይ ንስሓን የሠራኸው ለጻድቅ አይደለምና አንተን ላልበደሉ ለአብርሃምና ለይስሐቅ ለያዕቆብም አይደለምና፤ ወደ እኔ ወደ ኃጢአተኛው ንስሐ ተመለስ እንጂ። ከባሕር አሸዋ ቁጥር ይልቅ በድያለሁና። ኃጢአቴም ብዙ ነውና፤ ከበደሌም ብዛት የተነሣ የሰማይን ከፍታ አይ ዘንድ ላንጋጥጥ አግባቤ
አይደለም። በእግር ብረት ደከምኩ ነፍሴን ከኃጢአቴ አሳርፋት ዘንድ በዚሁም አላረፍሁም፤ ቍጣህን አነሣሥቻለሁና፤ ክፉውንም በፊትህ ሠርቻለሁና ክፉውንም ስጠብቅ የማይረባኝንም ሳበዛ። አሁንም በልቡናዬ ጉልበት እሰግዳለሁ፤ የአንተን ምህረት እየለመንኩ አቤቱ ጌታዬን በደልኩ ኃጢአቴንም እታመናለሁ። እማለላለሁ እለምንህማለሁ። ይቅር በለኝ አቤቱ ይቅር በለኝ። ለኃጢአቴም አሳልፈህ አትስጠኝ። ለዘላለምም ክፋቴን አትጠባበቀኝ፤በምድርም ጥልቅ ውስጥ አትበቀለኝ፤ አቤቱ አንተ ንስሐ የሚገቡ ሰዎች አምላክ ሆይ፤ ቸርነትህ በእኔ ላይ ይገለጽ ዘንድ አግባቤ ሳይሆን በቸርነትህ ብዛት አዳንከኝ። በሕይወቴ ዘመን ሁሉና በጊዜው ሁሉ አመሰግንሃለሁ። የሰማዮች ሠራዊት ሁሉ አንተን ያመሰግናሉ። ለዘላለምም ምስጋና ለአንተ ይገባል አሜን በእውነት።
ውዳሴ አምላክ ዘሰኑይ የአምላክ ምስጋና
አምላኬ ሆይ ሰውሬ የሠራሁትን ሁሉ ኃጢአት አንተ ታውቀዋለህ ኵላሊትንም ልቡናንም የምትመረምር አንተ ነህ፤ ሠውሬ የሠራሁትን የሥራዬን ክፋት አንተ ታውቃለህ፤ክፉ ሥራዬን አይተህ በእኔ ለመፍረድ የማትቸኩል፤ ከተድላዬ የማታዋርደኝ አንተ ነህ፤በወደቅሁም ጊዜ አካሄዴን የማታዋርድ አንተ ነህ፤ በጎ አድራጊ ይቅር ባይ ሆይ አትቸኩልም፤ አንተስ ጉስቁልናዬን አይተህ ታገስኸኝ መመለሴንም እየጠበቅህ ትዕግሥትህን አበዛህልኝ እኔም ከእንቅልፌ ነቅቼ ይቅርታህን ስፈልግ ወደ አንተ ገሠገሥኩ፤ ንስሐ የሚገባውን ሰው ንስሐውን እንድትቀበለው አውቄ በአለኝታህ ጸንቼ ወደ አንተ ገሠገሥኩ፤ የተናቅሁ ድኃ እኔ እለምንሃለሁ ከመውደቄ ታነሳኝ ዘንድ፤ኃጢአቴንም ትተላለፋት ዘንድ ንስሐዬንም ትቀበለኝ ዘንድ፤ ከመዓርጌ አዋርዶ ስለጣለኝ ጠላት እንዳይመካ ሳትነፍግ ሳትሳሳ የምትሰጥ፤ በጎ አሳቢ ቸር ጌታችን ፈጣሪያችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፤አንተ በታመነ ቃልህ በክቡር ወንጌልህ «እሹ ታገኛላችሁ
ለምኑ ይሰጣችኋል፤ ደጅ ምቱ ይከፈትላችኋል» ብለህ ተናግረሃልና ማቴ ፯፥፯ አቤቱ ችጋረኛ ድኃ የምሆን እኔም እውነተኛ ነገርህን አለኝታ ተቀብዬ በቃልህ ጸንቼ ኃጢአቴን አምኜ እየማለድሁ እነሆ በፊትህ ቁሜአለሁ። አምላኬ መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ አለኝታዬን ቆርጠህ እንዳታሳፍረኝ እለምንሃለሁና በደካማነቴ ራርተህ ኃጢአቴንም ይቅር ትለኝ ዘንድ፤ፊትህንም ከኔ እንዳትመልስ፤ ጸሎቴም አፍራ እንዳትመለስ። ያን ጊዜ አንተን ለመለመን የማልበቃ ኃጥእ በደለኛ እሆናለሁ፤ያደፍኩ የረከስኩ ነኝና። ነገር ግን በይቅርታህና በቸርነትህ ብዛት የፍጥረትህን ዕርቅና መዳንን በመውደድህ ነገሬን መልስልኝ ልቅሶዬንም ተቀበለኝ። ጌታዬ ፈጣሪዬ ሆይ የሥራዬን ክፋት የኃጢአቴን ብዛት አይተህ ዕንባዬን አታሳፍረኝ እንደ እውነተኛ አለኝታህ በክቡር ስምህ እንደ ማመኔ ይደረግልኝ እንጂ። የነጻች የእጅህ ሥራ የምሆን እኔ ከባሮችህ ወገን ነኝና እኔም በክቡር ምሳሌህና በመልክህ ተፈጥሬአለሁና በጥበብህ ከፈጠርካቸው ከባሮችህ
ወገን ስለሆንኩ ስለዚህ ደግፌ የረከሰች አንደበቴን ገልጬ እለምንሃለሁ። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ኃጢአቴንም ይቅር ትለኝ ዘንድ ንስሐዬንም ትቀበል ዘንድ ጽኑዕ ሥልጣን ከሃሊነት ያለህ ቸር ሆይ፤ ጐስቋላ ድኃ የምሆን እኔን በይቅርታህ እንድታድነኝ፤ በቸርነትህ ታደገኝ፤ የበዛች ኃጢአቴንም በደሌንም አርቅልኝ፤ እኔ የተከዝኩ በደለኛ ነኝና። አቤቱ በምለምንህም ጊዜ ፊትህን ከኔ ከባሪያህ አትመልስ፤አቤቱ ወደ አንተ በለመንሁ ጊዜ ይቅርታህን አታርቅብኝ። የጌቶች ጌታ፤የንጉሦች ንጉሥ ሆይ፤ ወደ አንተ የሚመለሱትን ዕርቅ ትወድዳለህና፤የሥጋና የነፍስን ደኅንነትንም ትወዳለህና። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የቀናች ሃይማኖትንና እውነተኛ መመለስን ስጠኝ፤ የጸራች ንስሐንም ትሰጠኝ ዘንድ እለምንሃለሁ። የሚጠሉኝ ጠላቶቼ የከፉ አጋንንት ድንገት በሚመጡበት ጊዜ አድነኝ። ነፍሴ ከሥጋዬ በምትለይበት ጊዜ ወደ አንተ አቅርበኝ እንጂ ከአንተ ወደ ሌላ አሳልፈህ አትስጠኝ። ሁሉ የሚቻልህ ፈጣሪ ሆይ፤ ጠላቶቼን በኔ ላይ
አታሰልጥናቸው፤አታሰናብታቸውም። ፈጣሬዬ ጌታዬ አዛኝ ይቅር ባይ የይቅርታና የቅንነት መዝገብ እግዚአብሔር ሆይ ሕይወትን የምትሰጥ፤በጐ ነገርን የምትወድ አንተ ነህና ስለዚህ ከክፉ ጠላቶቼ አድነኝ እሳቸውን ከመፍራት የተነሣ ነፍሴ ትንቀጠቀጣለችና፤ ያለ ክቡር ስምህና ያለ አንተ ለዘላለሙ ደኅንነት የለኝም አሜን በእውነት።
የዳዊት መዝሙር ፮
አቤቱ በቍጣህ አትቅሠፈኝ በመቅሠፍትህም አትገሥጸኝ። አቤቱ ድውይ ነኝና ይቅር በለኝ አጽንቶቼም ታውከዋልና ፈውሰኝ ነፍሴም ፈጽማ ታወከች፤አቤቱ አንተስ የምትታገስ እስከ መቼ ነው። አቤቱ ተመልሰህ ነፍሴን አድናት፤ ስለ ቸርነትህም አድነኝ፤ በሞት ጊዜ የሚያመሰግንህ የለምና በሲኦልስ የሚያምንብህ ማነው በትካዜዬ ደክሜአለሁ ሌሊቱንም ሁሉ አልጋዬን አጥባለሁ ምንጣፌንም በዕንባዬ አራስኩ፤ ዐይኔም በኃዘን ተበላሸች፤በጠላቶቼም ሁሉ ዘንድ አረጀሁ፤ ዓመጽን የምታደርጉ ሁሉ ከእኔ ራቁ እግዚአብሔር የልቅሶዬን ቃል ሰምቷልና፤እግዚአብሔርም ልመናዬንም ሰምቷልና፤እግዚአብሔር ጸሎቴንም ተቀብሏል፤ጠላቶቼም ሁሉ ይፈሩ ይዋረዱ፤ ወደ ኋላቸው ይመለሱ ፈጥነውም ፈጽመው ይዋረዱ።
ውዳሴ አምላክ ዘሠሉስ ስለ ሥጋ ወደሙ ቅዱስ ቍርባን
አምላኬ መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በዚህ በቅዱስ ቍርባን በሥጋ በደም መለኮት እንዳለህ አውቃለሁ። ይህንንም ስላወቅሁ ከክብር ሁሉ የከበረ ሥጋህን ከሰማያዊ ክብሩ ሁሉ ጋራ አከብርሃለሁ፤በዚህ በሚታየው ኅብስት መልክ እንድቀበል አምናለሁ። ከክብር ሁሉ የከበረ ደምህን ከሰማያዊ ክብሩ ሁሉ ጋራ አከብራለሁ፤ በዚህ በሚታየው ወይን መልክ እንድቀበል አምናለሁ፤ስግደት የሚገባው ግሩም መለኮትህንም እንድቀበል በፍጹም ልብ አምናለሁ። እንዲህም ከሆነ አንድ ቀን ፈጣሪዬን ጠባቂዬን ፈራጂዬን መድኃኒቴን እቀበላለሁ ዳግመኛም ይህንን ቅዱስ ቍርባን በኅብስትና በወይን አካል እንደማገኘው ምናለሁ፤ኅብስትና ወይን መሆን እንደሌለበትም አምናለሁ። የዓለም ሁሉ ፈጣሪ በመንግሥተ ሰማይ ኪሩቤል ሱራፌል የሚሰግዱልህ አንተ ነህ፤ ንጉሠ ነገሥት አንተ ተሠውረህበት እንዳለህ አውቄ አምኜ እቀበለዋለሁ። አምላኬ ሆይ ይህ ቃል እንደተናገርከው ነውና፤ ያንተ ቃል ነው እንጂ የሌላ ቃል አይደለም ያንተ ቃል ስለመሆኑ እናታችን ቤተክርስቲያን የምታምነውን ሁሉ አምናለሁ፤ እውነተኛ ምሥጢር አይደለም ለሚለኝ ነፍሴን ለሞት እሰጥበታለሁ። አምላኬ ሆይ እኔ የማይገባኝ የምድር ትል ስሆን አንተን አምላኬን ልቀበል እንዴት እችላለሁ። መላእክት የሚሰግዱልህ የዓለም ሁሉ ጌታ የሰዎች ሁሉ መሰብሰቢያ አንተ ነህ በአንተ ፊት ከንቱ ነገር የምመስል ነኝ፤ አንተ ግን ግሩም አምላክ ነህ፤እንዲህ ስትሆን አንተን ልቀበል እንዴት እችላለሁ።መቀበሌስ ይቆይና አንድ ጊዜ ስንኳ ዓይንህን መልሰህ ልታየኝ በእውነት የማይገባኝ ነኝ። ጌታዬ ሆይ አንተስ ከሰማይ የወረድህ ከኔ ጋር ልትገናኝ እኔን ደስ ልታሰኘኝ ሥጋህን ደምህን ልትመግበኝ መጣህልኝ። ነገር ግን ምንም አንተ እንዲህ ባለ ቸርነትህ ብትመጣልኝ እኔ ስለ ክፋቴ ብዛት አንተን ልቀበል በእውነት የማይገባኝ እንደሆንኩ አምናለሁ እታመናለሁ። ዳግመኛም እኔ ባንተ ፊት የተዋረድሁ ረብህ ጥቅም የሌለኝ ፍጡር ነኝ። ረብህ ጥቅም የሌለኝ ፍጡር ብቻ ስንኳ አይደለሁም። ሕግህን ያፈረስሁ ታላቅ ኃጢአተኛ ነኝ እንጂ፤ጌታዬ አንተ ታውቀኛለህና ምን እነግርሃለሁ? በአንተ ስንት ጊዜ ሸፈትሁ የሸፈትሁበትም ጊዜ ቍጥር የለውም። የነፍሴ ጌታ የነፍሴ ንጉሥ አንተ ብቻ ስትሆን በሽፍትነቴ ብዙ ጊዜ ከነፍሴ አስወጥቼ ሰድጄሃለሁ። በአንተ ቦታ ስለአንተ ፈንታ ያንተንና የኔን ጠላቶች ዛሬ አግብቼ አኑሬአለሁ፤አግብቼ ያኖርኋቸውም የአንተና የእኔ ጠላቶች ሰይጣንና ኃጢአት ናቸው። አንተ ግን ምሕረት ልማድህ ነውና እኔ እንዲህ ያለ ክፋት ሳደርግብህ እየኖርሁ ክፋቴን ሁሉ ሳታስብ በመሐሪነትህ ወደኔ ትመለሳለህ ዕድሜን ለንስሐ ትሰጠኛለህ። ራስህንም ሰጥተህ በነፍሴና በሥጋዬ ባለቤት ትሆናለህ ይህንንም ሁሉ ማድረግህ ለኔ ፍቅርህን ለማብዛት ብቻ ነው እንጂ ከኔ ትርፍ ነገር አገኛለሁ ብለህ አይደለም። ፍቅርህንስ ለማብዛት ካልሆነ ፍጥረትህ ሁሉ በአንተ ፊት ጻድቅ አይደለም፤የመላእክት ሁሉ ጻድቅነት ስንኳ የኔ ብቻ ቢሆን ጻድቅነቴን አስበህ አንተ ወደኔ ልትመጣ አይገባኝም ነበር እኔም አንተን ልቀበል የሚገባኝ አይደለሁም።ጌታዬ ሆይ አንተን የዘላለም ንጹሕ እንደሆንክ ሳውቅ አሁን በደካማ ልቤ በወስላታ አንደበቴ ክፋት አንድ ሰዓት ስንኳ በማይለየው ልቤ አንተን ልቀበል እንዴት እችላለሁ። ነገር ግን የማይገባኝ እንደሆንኩ አምናለሁ እታመናለሁ። ሰውን የፈጠርህ ሆይ በወሰንከው ሥርዓት ከፊትህ እቆም ዘንድ አጽናኝ ነፍስን የተከልክ
አጽንቶችን ያለመለምክ ጌታዬ ሆይ የሥራዬን ክፋትና ኃጢአቴን አታስብ። ያፈርሁ የተዋረድሁ እኔ በፊትህ እፈራለሁና ወደ ይቅርታህ ትጠራኝ ዘንድ ተስፋህን አቆየኝ። አቤቱ ስምህን ለካደ የሠራኸውን አስብ ከካደህ በኋላ ከገሃነም አውጥተህ ተድላ ወደሚደረግበት ወደ ገነት መለስከው፤ ተስፋውንም ካንተ አልቆረጠም፤ ችግረኛ የምሆን የኔን የክፉ በደሎቼን ሠውር የኃጢአቴንም መጋረጃ ቅደድ የፊቴን ጥቍረት በእውነተኛ የፍርድ ቀን መጻሕፍት በፊትህ በተገለጹ ጊዜ አታሳፍረኝ። አቤቱ በፍጥረትህ ሁሉ በምትፈርድበት ጊዜ በፊትህ ያፈርሁ የተጨነቅሁ አንደበተ ዲዳ ነኝና ከአንተ ልለምን ልማልድ አልደፍርም ስለዚህ አታሳፍረኝ። አቤቱ እኔ ደስ አላሰኘሁህምና በፊትህም ጥቂት ስንኳ በጎ ነገር አላደረግሁምና በክፋቴ ብዛት በአእምሮዬ ማነስ አፌ ረክሳለች። ሸታለች እንጂ። በረከሰች አንደበቴ እናገራለሁ ያደፈ ፊቴንም ወደ አንተ አቀናለሁ ይቅር እንድትለኝ ወደ አንተ እለምን እማልድ ዘንድ እኔ ፍጥረትህ ነኝናበምታስፈራ በምታስደነግጥ በግርማ መለኮትህ በተገልጽህ ጊዜ ኃጢአትን ተመልቼ ከፊትህ ሳልቆም መላእክት አንተን ለማመስገን አንተን ለማድነቅ በወረዱ ጊዜ በገናና ስምህ ስላመኑ በመከራ በመገዛት የነበሩ ሰዎች ሁሉ ሕዋሳት ይሰበሰቡ ዘንድ በነጋሪት በተጠሩ ጊዜ ፍጥረትም ሁሉ የኃጢአት ሸክም ተሸክሞ በሚያስፈራ
ዙፋንህ ፊት በሚቆሙበት ጊዜ የሠሩትን ክፉውንም በጎውንም ሁሉ ያን ጊዜ ሥራችን ይታወቃል። ምሥጢራችንም ይወጣል። መጋረጃችንም ይገለጣል። አቤቱ የኃሣራችንና የኃፍረታችን ደብዳቤ በመላእክት ፊት ይዘረጋል። ሥራችን ሁሉ በፍጥረት ሁሉ መካከል ይነበባል። አቤቱ ጌታዬ ሆይ የዚያች ሰዓት ግርማዋ ምን ያህል ይሆን፤ በሚያስፈራ በሚያስደነግጥ ዙፋንህ ተቀምጠህ በታየህ ጊዜ ክብርህም በፊትህ በተገለጠ ጊዜ የፈጠርከውን ፍጥረት በቅንነትና በእውነት በገዛህ ጊዜ የተሠወረውም ሁሉ በታየ ጊዜ ጻድቃንም ከኃጥኣን በሚለዩበት ጊዜ። አለኝታ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የመከራዋ ግርማ ሊያዩት ስለሚያስጨንቅ ስለዚያች ሰዓት ይቅርታህን እፈልጋለሁ። በፊትህ በሠራሁት ኃጢአቴ ከባሪያህ ጋር አትከራከር። በይቅርታህ ነው እንጂ ከፍርድህ መዳን የሚቻለው የለም። አቤቱ ጌታዬ መምህሬ ሆይ ከዚህች ከምታስጨንቅ ፍርድ አድነኝ። የሕይወት ያይደለ ፍርድ፤ ከሷ ስለመጣበት ሰው ሁሉ የሚጨነቅባት፤ አሁንም ጌታዬ ሆይ ነፍሴን ከዚያች ሰዓት ታድናት ከገሃነም ፍርድም ታድነኝ ዘንድ እለምንሃለሁ። በለጋስነትህና በቸርነትህ በርኅራኄህ ከወዳጆችህ ጋራ ትቆጥረኝ ዘንድ አሜን ይደረግልኝ። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ እለምንሃለሁ ይቅርታህን በላያቸው ካፈሰስክ በመከራቸው ከወደድሃቸው ጋር ዕድል ትሰጠኝ ዘንድ ለእኔስ በፊትህ ለመቆም ለይቅርታህ የሚስማማ በጎ ሥራዬ አይታየኝም። በይቅርታህ እታመናለሁ እንጂ። በበጎ ሥራቸው ላገለገሉህና ለሚወዱህ ለነገርሃት ለዘላለም ደስታ በለጋስነትህ የበቃሁ ታደርገኝ ዘንድ ጌታዬ ሆይ የጠቆርኩ የረከስኩ እኔን ይቅር በለኝ። አቤቱ ምሳሌው ወደማይነገር ብርሃን አግባኝ፤ የጠቆረ ፊቴንም በእውነተኛ ንስሐ እሳት በፈላ ዕንባ እጠበኝ አሜን በእውነት ይደረግልኝ።
የዳዊት መዝሙር ፳፬
አምላኬ ሆይ ነፍሴን ወዳንተ አነሳሁ። አቤቱ ባንተ አምኛለሁና ለዘላለሙም አልፈር። ጠላቶቼም ደስ አይበላቸው በአንተ ያመኑ ሁሉ አያፍሩምና፣ዘወትር የሚበድሉ ግን ይፈሩ። አቤቱ መንገድህን አመልክተኝ ፍለጋህንም አስተምረኝ በቸርነትህም ምራኝ፤ አንተ ኃይሌ ነህ መድኃኒቴም ነህና እዘንልኝ፤ዘወትርም አንተን ተስፋ አደርጋለሁ አቤቱ ይቅርታህን አስብ፤ቸርነትህም ለዘላለም ነውና፤ባለውቀቴና በልጅነቴ ጊዜ የነበረ ኃጢአቴን አታስብብኝ፤አቤቱ ስለ ቸርነትህ እንደ ይቅርታህ አስበኝ እንጂ፤ እግዚአብሔር ቸር ነው ቅንም ነውና ስለዚህ የሚስቱትን መንገድን ይመራቸዋል፤ለቅኖችም ፍርድን ያስተምራቸዋል፤ ለግሮችም መንገድን ያመለክታቸዋል ኪዳኑንና ምስክሩን ለሚጠብቁ፤የእግዚአብሔር መንገድ ይቅርታና እውነት ነው፤ አቤቱ ኃጢአቴ ብዙ ነውና ስለ ስምህ ይቅር በለኝ፤ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ማነው እሱም የመረጠውን መንገድ ይመራዋል፤ነፍሱም በመልካም ቦታ ታድራለች ዘሮቹም ምድርን ይወርስዋታል፤እግዚአብሔርን ለሚፈሩ ኃይላቸው ነው፤ ለሚጠሩትም እግዚአብሔር ምስክራቸው ነው። ሕጉንም ያስተምራቸዋል፤ዓይኖቼም ዘወትር ወደ እግዚአብሔር ናቸው፤ እሱ እግሮቼን ከወጥመድ ያወጣቸዋልና፤ወደ እኔ ተመልክተህ ይቅር በለኝ፤ብቸኛ ነኝ ችግረኛም ነኝና፤የልቤ ኀዘኑ ብዙ ነውና ከመከራዬ አድነኝ፤መከራዬንና ድካሜን እይ፤ኃጢአቴንም ሁሉ ይቅር በለኝ፤ጠላቶቼም እንዳይበዙ እይ፤ በግፍ ይጠሉኛል፤ነፍሴን ጠብቀህ አድነኝ፤ በአንተም አምኛለሁና አልፈር፤ፍጹምነትና ቅንነት ይጠብቁኝ፤ አቤቱ አንተን ተስፋ አድርጌአለሁና፤እግዚአብሔር እስራኤልን ከመከራው ሁሉ ያድነዋል።
ውዳሴ አምላክ ዘረቡዕ የንስሐ ጸሎት
አምላኬና ጌታዬ ሆይ አንተ ከኔ ከራቅህ እኔ አንተን ካልተቀበልሁ ሌላ ሕይወት አይገባኝምና አቤቱ እንዴት ባለ ገደል እወድቃለሁ ይሆን? እንደምንስ ባለ መከራ ተይዤ እጨነቃለሁ ይሆን? የልቤን ክፋት የልቤን ወስላትነት የሚያጠፋ መድኃኒት ካንተ ካላመጣሁ ከማን አመጣለሁ። ከጠላቶቼ የማመልጥበትን መማጸኛ ካንተ በቀር ማን አለኝ። የሰጠኸኝንስ ጸጋ በልቤ የሚያኖርልኝ ሌላ ማን አለ አንተ አይደለህምን። ኢየሱስ ሆይ አንተ የኔን ሥጋ ካልበላችሁ የእኔን ደም ካልጠጣችሁ በላንተ ሕይወት የለም አልህ። እንዲህም ካልህ በነፍሴና በሥጋዬ እንዳልሞት ይገባኛል ሳልል በግድ ወደ ቍርባን እቀርባለሁ። ዳግመኛም አንድ ክፉ ልጅ በረኀብ በተጨነቀ ጊዜ «እንደዚህ በረኀብ እንዳልሞት ተነስቼ ወደ አባቴ ልሂድ አባቴንም በድዬዋለሁና ከባሮችህ እንደ አንዱ አድርገኝ እንጂ ልጅህ ልባል አይገባኝም ልበል» ብሎ አስቦ ወደ አባቱ እንደሄደ አባቱም በሩቅ ባየው ጊዜ በርኅራኄ በፍቅር እንደተቀበለው ተናግረሃልና ሉቃ. ፲፭፥፲፩-፴፫
እኔ በዚህ ምክንያት እንደርሱ ሁሉ በእግረ ንስሐ ተነሥቼ ወደ አንተ ወደ ርኅሩኅ አባቴ እመጣለሁ፤ወደ አንተ ወደ ኃይሌ እመጣለሁ፤ ወደ አንተ ወደ ጠባቂዬ እመጣለሁ፤ ወደ አንተ ወደ መማጸኛዬ እመጣለሁ፤ ወደ አንተም አሥነስቶ የሚያመጣኝ «ኑ ብሉ ብለህ አስጠራኻቸው፤» በቀሩ ጊዜ በወንጌል የተናገርኸው ቃል ነው፤ ማቴ. ፳፪፥፩-፲፬ ዳግመኛም ወደ አንተ መምጣት እንዳልፈራ ልቤን የሚያጽናናልኝ እውቀቴንም የሚጨምርልኝ ከኔ ክፋት የሚበልጥ የአንተ መሐሪነት ነው። ፈሪሳውያንንም «ኃጢአተኞችንም ይቀበላል ከኃጢአተኞች ጋራ ይበላል» ቢሉህ ነቀፋቸውን ፈርተህ ኃጢአተኞችን መቀበል እንዳልተውህ ከእርሳቸውም ጋር መብላትን እንዳልተጸየፍህ በወንጌል ተጽፎ አለ። ማቴ. ፱፥፲-፲፫ ይህም እውነት ከሆነ የኃጢአተኞች አለቃ እኔ ነኝና ወደ አንተ ስቀርብ እንዳትጸየፈኝ አውቄ ብቀርብ በደምህና በሥጋህ ነፍሴንና ሥጋዬን ከኃጢአት እንድታነጻልኝ ተስፋ አለኝ። ልቤን እንደ እሳት የሚያቃጥለኝን ኃጢአት ሁሉ እንድታጠፋልኝ ተስፋ አለኝ። የቸርነትህ ድልብ አያልቅምና ለአንተ የምከፍልህን ዕዳ እንድትተውልኝ ተስፋ አለኝ። በለጋሥነትህ የከበርህ ነህና ልቤን ባለጸጋ የሚያደርግልኝ ጸጋ፤ ከገሃነመ እሳት የሚያድነኝ ጸጋ ወደ መንግሥተ ሰማያት የሚያገባኝ ጸጋ እንድትሰጠኝ ተስፋ አለኝ። አምላኬና ጌታዬ ሆይ፤ፈጣሪዬ ሆይ እለምንሃለሁ፤ ከኃጢአቴ ባሕር ማዕበል ታድነኝ ዘንድ ከመሰናክሌም፤ ደቀ መዝሙርህ ጴጥሮስን ከመዋረዱ ጽናትና ከባሕር ድንጋጼ እንደ አዳንኸው፤ ከፍ ከፍ ባለች ክንድህና በጸናች ቀኝህ ከመሠጠምም እንደ አዳንኸው፤ማቴ. ፲፬፥፳፰-፴፫ ሐዋርያህ ጳውሎስንም እንደተቀበልከው አንተን ከካደ ምዕመናንንም ከተጣላ በኋላ የዲያቆናት አለቃ የሰማዕታት መጀመሪያ እስጢፋኖስንም ለመግደል ከከተማ ከወጣ በኋላ ከዚህ ሁሉ በኋላ በቅዱሳንህ ጉባዔና በቤተ ክርስቲያንህ ዘንድ ለወገኖችህ በስምህ የሚያስተምር የከበረ ታላቅ መምህር እንዳደረግኸው። የሐዋ.ሥራ ፯፥፷ ፰፥፫ ፱፥፩-፴፩ ፲፫፥፪-፲፪ ፲፱፥፲፩-፳
ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ እንደዚህ ሁሉ ከቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የራቅሁ እኔን ተቀበለኝ ከይቅርታህም አታርቀኝ። ቸርነትህንም ለዘላለሙ አትንሳኝ። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የመፃጉዕን ኃጢአት ይቅር እንዳልኸው በሥልጣንህም ከሃሊነት በብዙ አሕዛብ ፊት ተግቶ አልጋውን ተሸክሞ እንዲነሣ እንደ አደረግኸው ዮሐ.፭፥፪-፱ እንደዚህም ሁሉ ኃጢአቴን ይቅር ብለህ ለኔ ለባሪያህ የሥጋና የነፍስን ሕይወት ስጠኝ። አባቴ ሆይ በክብር ስም ስለተጠራሁ በደኅንነቴ ወራት ሁሉ በጎ አገዛዝ እገዛልህ ዘንድ አምልኮትህን አጽናልኝ። ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ ለዘላለሙ የምትኖር ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ አቤቱ የከነናዊትን ልመና እንደሰማህ ታማ ሥቃይ ጸንቶባት ከነበረች ከልጅዋ ጋኔን እንዳወጣህ «ሃይማኖትሽ ታላቅ ነውና እንደ ፈቃድሽ ይደረግልሽ» እንዳልኻት ፈውስንም እንደሠጠኻት ማቴ. ፲፭፥፳፩-፳፰ ጌታዬ ሆይ ጎስቋላ ችግረኛ የምሆን እኔንም እንዲሁ እለምንሃለሁ። ከንቱውንም ዓለም በመመኘት የሚከራከረኝ ሰይጣንን ከኔ ታርቀው ዘንድ በየጊዜ ሁሉ ፈቃድህን እንድሠራ በቸርነትህ ትረዳኝ ዘንድ አሥራ ሁለት ዓመት ደም ሲፈሳት የነበርችውን ሴት እንደ አዳንካት በአንተ ስለ አመነች ከደዌዋ አድነህ ሕይወትን እንደሠጠኻት ማቴ.፱፥፳-፳፫ እንደዚህም ሁሉ እኔንም ከደዌዬ ፈውሰኝና ሃይማኖቴን ስጠኝ፤ ከኃጢአቴም አንጻኝ። በሕወቴም ወራት ሁሉ በእውነት አመልክህ ዘንድ ክቡር ስምህንም እስከ ዘላለም አስተምር ዘንድ። አሜን በእውነት። አቤቱ ፍጥረትህን ሁሉ ያሳደፈች ኋላ ወደ ጽሩይ ንስሐ የተመለሰች ዘማን ይቅር እንዳልኻት ስለመመለሷና ስለ ልቅሶዋ ስለ ሐዘኗም «ኃጢአትሽ ተሠርዮልሻል በፍቅር ሂጂ» እንዳልኻት ዮሐ. ፰፥፫-፲፩ አቤቱ እንደዚህ ሁሉ የበዛ የሚያቃጥል እንባን ስጠኝ። ባለሁበት ዘመን ሁሉ ከዓይኔ ይፈስ ዘንድ ምናልባት ከእድፌ ጥቂት ያጥብልኝ እንደሆነ። አቤቱ በቸርነትህም የፊቴን ጥቍረት ያነጻልኝ እንደሆነ ከወገኖችህም ወገን እንደማያውቅህ አድርጎ ከካደህ በኋላ በመመለሱና በመጸጸቱ፤ በመረረ ኀዘኑም ጊዜ የሐዋርያት አለቃ የሚሆን የጴጥሮስን ንስሓ እንደ ተቀበልክ በምዕመናንም ላይ እንደ አንተ ያለ አለቃ አድርገህ እንደ ሾምከው ቤተ ክርስቲያን የምትታነጽበት የሃማኖት መሠረት አድርገህ የመንግሥተ ሰማያት መክፈቻ እንደ ሰጠኸው ማቴ. ፲፮፥፲፯-፳ አቤቱ እኔንም እንደርሱ ተቀበለኝ። በዘመኔ ሁሉ ወደ አንተ እመለስ ዘንድ እጸጸትም ዘንድ የሠራሁትንም ኃጢአት ይቅር ትለኝ ዘንድ ስለ ክቡር ስምህና ስለ መልካም ስምህ ይቅር በለኝ። የቀራጩንም ኃጢአት ይቅር እንዳልከው ሃይማኖቱን እንደ ተቀበልከው። ከፈሪሳዊ ይልቅ የተመረጠና የነጻ እንደ አደረግኸው ስለ ትሕትናውም እንደ አከበርከው ሉቃ. ፲፰፥፱-፲፬ ጌታዬ ሆይ ዘወትር በፊትህ በደሌን አምን ዘንድ የነፍሴን ትሕትና ስጠኝ። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በመስቀል ላይ ሳለህ እውነተኛ የባሕርይ አምላክ እንደሆንህ ስለ አመነብህ ቀማኛውን እንደ ተቀበልኸው «ለሁሉም እንደ ሥራው ትከፍለው ዘንድ በምትመጣበት ጊዜ አቤቱ በቸርነትህ አስበኝ» ስለ አለህ ለሰው ሁሉ የምታዝን ይቅር ባይ ሆይ እንዲህ ባለህ ጊዜ «ዛሬ ከኔ ጋራ በገነት ትኖራለህ» አልከው በኃጢአቱ በመገደሉ በክፉ ሥራውም ቸል አላልከውም፤አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን የተዘጋ ገነትን ፈጥነህ ከፈትህለት እንጂ፤እሱ ካሰበው ይልቅ ፍጹም ጸጋን ባለሟልነትን ከአንተ ሰጠኸው። ሉቃ. ፳፫፥፵-፵፫ ኃጥእ በደለኛ የምሆን የእኔንም ሰውነት ለዘላለሙ ወደ ምኖርበት ወደ ሰፊ ይቅርታህ አግባት። ኃጢአቴን ይቅር በለኝ በደሌንም በይቅርታህ ተላለፈው። አሜን ይደረግልኝ።