የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት

✥ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ እዚህ በመጫን ያንብቡ

✥ ፹፩ (81) መፅሐፍ ቅዱስ እዚህ በመጫን ያንብቡ

✥ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት_የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክና ትርጉም እዚህ በመጫን ያንብቡ

✝የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መግቢያ ✝

ክፍል አንድ

መጽሐፍ ቅዱስ ምንድነው? 🗝

መጽሐፍ ቅዱስ ቃሉ እንደሚያመለክተው መጽሐፍ እና ቅዱስ የሚሉ የሁለት ቃላት ጥምረት ነው ፡፡

★“መጽሐፍ” ለሚለው ምንጭ በግሪክ ቋንቋ ቢብሎስ (byblos) ከደንገል በተሠራ ወረቀት ወይም በብራና ከተጻፈ በኋላ በሁለት በትሮች የሚጠቀለል መጽሐፍ ያመለክታል፡፡ ይህ ስም ቢብሎስ (byblos) ከተባለ ከተማ ስም የተገኘ ነው ፤ እርሱም ከኒቂያ ወደቦች መካከል በቤይሩት 25 ማይል ያህል ርቆ የሚገኝ አገር ነው ፡፡ ለመጽሐፍ ያገለግል ዘንድ ፓፒረስ (ደንገል) የተባለውን ተክል እንደ ወረቀት አድርገው ይሠሩበት የነበረ ቦታ ነው ፡፡ቢብሎስ በእንግሊዘኛው ባይብል ተብሎ ሲተረጎም በአማርኛው ደግሞ መጽሐፍ በሚለው የግብር ስም ቃል ተተረጐመ ፡፡

★“ቅዱስ” (holy)የሚለውን ስናይ ደግሞ ልዩ፣ክቡር ለእግዚአብሔር የተለየ ማንኛውንም ነገርን ያመለክታል፡፡እግዚአብሔር በራሱ ከፍጥረታት ልዩ ነው፣ ከጣኦታት የተለየ ነው መንፈሱም(ሐሳቡም) ከክፋት ሐሳብ የተለየ ስለሆነ ቅዱስ ነው፡፡ጠቅለል አድርገን ስናየው ስለ ቅዱሱ እግዚአብሔር ያለፈውም መጪውም ስራ፣በመረጣቸውና ባመኑበት ሰው ልጆች ላይ ያደረገውንና ያለው ሐሳቡ ፈቃዱ ወዘተ ላይ የሚያወራ መጽሐፍ ስለሆነ ቅዱስ መጽሐፍ ተብሏል፡፡በእንግሊዘኛውም “holy bible” በማለት ይጠራል፡፡

☞ መጽሐፍ ቅዱስ ሁለት ክፍሎችን የያዘ ነው::የመጀመርያው ክፍል #ብሉይኪዳን ሲሆን የእግዚአብሔር የድሮው መሐላ(የአብርሐም ዘር እንደሚበዛና ከንአን ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ያለው ምድር እንደሚሰጠው በዘሩም አለሙ ሁሉ እንደሚባረክ)የሚገልጽ ሲሆን

✡ እግዚአብሔር ፍጥረታትን ከመፍጠሩ ጀምሮ ስለ ሰው ልጅ ከእግዚአብሔር ክብር መለየት አወዳደቅና በምድር ላይ መብዛት

✡በእግዚአብሔር ስለ ተወደደ አብርሐምና በዘሩ ዓለም እንደሚባረክ መሐላ

✡ስለ የያእቆብ ልጆች ወደ ግብጽ መሰደድና ከባርነት በእግዚአብሔር ድንቅ ረዲኤት መመለስ

✡ስለ እስራኤል መንግስት መመስረት መስፋትና የነገሥታቱ ታሪክ

✡መዝሙራትና ምሳሌያዊ የጥበብ ትምህርቶችን

✡ስለ ሰው ልጅ ወደ እግዚአብሔር ክብርና ፍቅር መመለስ ትንቢት  ማለትም እግዚአብሔር ዓለሙን እንደሚያድንና ስለ እስራኤል ህዝብ ትንቢቶችን ይዟል::

☞ሁለተኛው ክፍል ደግሞ #ሐዲስኪዳን ሲሆን ለአብርሐም በዘርህ አሕዛብ ይባረካሉ ያለውን ያ ዘር ክርስቶስ በስጋ ተገልጦ አለሙን በደሙ መስዋዕትነት ቀድሶ የሰውን ልጅ እንዳዳነ ያመኑበትም የእግዚአብሔር ልጆች የቅዱስ መንፈሱም ማደርያ ማድረጉን ለዓለሙ ሁሉ በደሙ በኩል አዲስ መሐላን ማድረጉ የሚገልጽ ሲሆን

❖ከእመቤታችን ብስራትና ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ጀምሮ ስላስተማራቸው ትምህርቶች ስላደረጋቸው ተአምራት ስለ ሰው ልጆች ሐጢአት ዋጋ ካሳ እንዲሆን መከራ መቀበሉ መሞቱ ሞትን ድል አድርጎ መነሳቱ ለብዙዎች መታየቱን ማረጉን #በወንጌላት

❖ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ እንደተቀበሉና በጌታችን ኢየሱስ ስም የሐጢአት ስርየት መስበካቸውን ብዙ መከራ መቀበላቸውንና ብዙዎችን ማጥመቃቸውን #በሐዋርያት ሥራ

❖ስለ ጌታችን ኢየሱስ ማንነት፣ስለ አዲሱ መሐላ፣ስለ አማኞች ስነ ምግባር በእምነትም ስለመጽናት ፣በክርስቲያኖች መኖር ያለበት ፍቅር #በመልእክታት

❖ስለ መጪዋ ቤተ ክርስቲያን፣ ዲያብሎስ በዚህ ምድር ስለሚኖረው የክፋት አሰራርና ስለ ቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች፣ስለ ሐሳዊው ክርስቶስና ስለ አዲሱ የአለም መንግስት አሰራር፣ ስለ ጌታችን ክርስቶስ ዳግም መምጣትና ስለዚህ አለም ማለፍ፣ስለ ክርስቲያኖች ተስፋ በአዲሲቷ ምድርና ሰማይ ከክርስቶስ ጋር ያለው ኑሮ #በራእይ ይዟል፡፡

በቀጣዩ የመግቢያ ክፍል መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ ጥራዝ መቼና እንዴት ተደረገ የሚለውን እናያለን

✞❀✞❀✞❀✞❀✞❀✞❀✞

“የመዳንንም ራስ ቁር የመንፈስንም ሰይፍ ያዙ እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ነው።”

(ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6:17፤)

✞❀✞❀✞❀✞❀✞❀✞❀✞

“የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የእግዚአብሔርም ፍቅር የመንፈስ ቅዱስም ኅብረት ከሁላችሁ ጋር ይሁን። አሜን።”

(2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 13:14፤)

ክፍል ሁለት

መጽሐፍ ቅዱስ መቼ በአንድ ጥራዝ ተጠቀለለ?

ከክርስቶስ ልደት በፊትም ይሁን በኋላ የተጻፉት ሁሉንም መጻሕፍቶች ለየብቻቸው ነበሩ፡፡ከ500ዎቹ ዓ.ዓ አጋማሽ ጀምሮ ማለትም እስራኤላውያን ከምርኮ ከተመለሱና ቤተ መቅደሱም ካነጹ በኋላ እዝራ መጻሕፍቶችን አሰባሰበ የአይሁድ መምህራንም (ረበናት)ጉባኤ አድርገው መጻሕፍቶቹን በማጥናት በአንድ ጥራዝ ባይጠቀልሉትም  39 የብሉይ ኪዳን መጻሕፍቶችን ለይተው አጸደቁ፡፡በኋላ በግሪክ ግዛቶች ይኖሩ የነበሩ አይሁዳውያን ዕብራይስጥ ስለማይችሉ በግሪክ እንዲተረጉሙላቸውና መጻሕፍቱ በቤተ መጻሕፍት ተተርጉመው እዲቀመጡ በንጉስ ትእዛዝ ዕብራይስጥና ግሪክኛ አቀላጥፈው የሚናገሩና የሚጽፉ 72(ሰባ ሊቃናት) ሰዎች ተመርጠው በ300ዓ.ዓ ገደማ ወደግሪክኛ ሲተረጉሙ ከ39 ሌሎች ተጨማሪ መጻሕፍትንም ጨምረው ተረጎሙ፡፡ነገር ግን ይህ በ90 ዓ.ም የግሪኮቹና የእየሩሳሌሞቹ አይሁዶች ከ39ኙ መጻሕፍት ውጭ በተጨመሩት ላይ ተነጋግረው በአንድ ሐሳብ ተስማሙ እሱም “የተዛባ የታሪክ አቀራረብና የሐሳብ መቃረን አለባቸው፣ከባቢሎን ስደት መልስ በኋላ ማለትም ከ539 ዓ.ዓ በኋላ ደግሞ እግዚአብሔር ነቢይ አልላከም የእግዚአብሔር ዝምታ ጊዜ ስለነበር በመንፈሱ መሪነት ተጽፈዋል ብለን አንቀበልም” በሚል 39ኙን አጸኑ፡፡

አንዳንድ ክርስቲያኖች ከሰባ ሊቃናቱ ግሪክኛ ቅጂ አይሁዳውያኑ ያልተቀበሏቸውንም ጭምር ይጠቀሙ ነበር፡፡ በብሉይ ኪዳን ማለትም የሙሴ ሕግ፣ መዝሙራትና ነቢያት  ስለ ክርስቶስ ስለሚመሰክሩ ይጠቀሙባቸው ነበር(ሉቃ 24፥44) ፡፡በአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ግን ምንም አገልግሎት አልነበረም የጋራ አምልኮም ቢሆን ትምህርት ሁሉም በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ብቻ እንጂ  በመጽሐፍ አልነበረም፡፡የኋላ ኋላ ግን በተለያየ ሁኔታና በተለያየ ምክንያት ወንጌልና መልእክታት ከ50-100 ዓ.ም ባሉት በተለያዩ ዓመታትና በተለያዩ ቦታዎች ውስጥ በሐዋርያቱ ተጻፉ፡፡መልእክታቱ ከአንዷ ቤተ ክርስቲያን ወደ ሌላኛይቱም ይተላለፉ ነበር ፡፡ ሐዋርያት በብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ላይ እንደ አይሁዳውያኑ የተወሰነ የመጻሕፍት  ቁጥር አላስቀመጡም፡፡ከሐዋርያት በኋላ ማለትም ከ100 ዓ.ም ወዲህ በሐዋርያት ሥም ብዙ መጻሕፍቶች ይጻፉ ጀመር ይህም ማለት የሐዋርያው እገሌ ወንጌል ወይም መልእክት እየተባለ ይጻፍ ነበር::በዛን ጊዜ የነበሩት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች በብሉይ ኪዳን ላይ የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ማለትም ወንጌላትና መልእክታት ወስነው እውቅና ለመስጠት በጣም ተቸገሩ ምክንያቱ በሐዋርያት ስም የተጻፉት መጻሕፍት ከመብዛታቸውና የሐሰት ትምህርቶችን ከመያዛቸው የተነሳ ብዙ ክርክር በማስነሳታቸው ነበር::የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ማለትም ወንጌላትና የሐዋርያት ትምህርት ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጋራ አንድ ላይ በማድረግ በሙሴ ሕግ በነቢያትና በመዝሙራት የተነገረለት መሲሕ ፍጻሜው በወንጌላትና በመልእክታት እንዴት እንደሆነ እያስማሙ አማኞችን ለማስተማር ለማንበብም እንዲያመች በአንድ ጥራዝ መሆን አስፈለገ::

✍የተገኙት መጻሕፍት ብዙ ጥናትና ምርምር ከተካሄደባቸው በኋላ ግን ቅዱስ አትናቴዎስ በስሩ ያስተዳድራቸው ለነበሩ የእስክንድርያ አብያተ ክርስቲያናት ከ39ኙ የአይሁድ ብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ላይ 27 የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት በማጽደቅ እንዲጠቀሙ ወሰነ::

✍የሎዶቅያ ሲኖዶስ በ364 ዓ.ም ከአይሁድ ቀኖና 22 የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት እንዲሁም ባሮክና የኤርሚያስ መልእክት በመጨመር ከ26 የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት(ራዕየ ዮሐንስን በማውጣት) ሲያጸድቅ

✍የካርቴጅ ሲኖዶስም በ397 ዓ.ም በአይሁድ ቀኖና ላይ አንዳንድ ተጨማሪ መጻሕፍትን በማስገባት 44 የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትና 27 የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት አጸደቀ::በጉባኤያቱ የአይሁዱ ብሉይ ኪዳን ቀኖና 39 ኙን መጻሕፍትና የአዲስ ኪዳን 27 መጻሕፍት የዶግማ መጻሕፍት ተብለው ሲጸድቁ ሌሎቹ ከሰባ ሊቃናት የተጨመሩ መጻሕፍትን ደግሞ የቀኖና መጻሕፍት በመባል ጸድቀዋል::በተጨማሪ የቀኖና መጻሕፍቱ ላይ በየዶግማዎቹ ላይ እንደተደረገው ጥልቅ ምርምርና ጥናት የማመሳከርም ስራ አልተደረገም በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት ያሉት የቀኖና መጻሕፍት የውስጣዊ ይዘት መለያየት የሚታይባቸው ለዚህ ነውና::

☞ቅዱሳት መጻሕፍትን የጻፉ ነቢያትና ሐዋርያት በተራ ጽሑፍ መልክ እንጂ ምዕራፍና ቁጥር አድርገው አልጻፉም ይህ መቼ ማንና ለምን አደረገው?

☞መጽሐፍ ቅዱስ የሰዎች ፈጠራ አለመሆኑ እውነተኛነቱ በምን ይታወቃል?

☞የአሁኑ መጽሐፍ ቅዱስ ከድሮው በዘመን ሂደት ተበርዟል?

የሚሉት የርዕሳችንና ከተከታታዮች የመጡልንን ጥያቄዎችን በቀጣዩ ክፍል እናያለን

❀✞❀✞❀✞❀

(ወደ ኤፌሶን ሰዎች  6)

———-

23፤ ከእግዚአብሔር አብ ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምና ፍቅር ከእምነት ጋር ለወንድሞች ይሁን።

24፤ ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ባለመጥፋት ከሚወዱ ሁሉ ጋር ጸጋ ይሁን፤ አሜን

ክፍል ሶስት

✨መጽሐፍ ቅዱስ በቁጥርና በምዕራፍ ማንና ለምን ከፈለው?

መጽሐፍ ቅዱስ በምዕራፍ መከፋፈሉ ከመጻሕፍቶቹ አንዱ ክፍል የያዘውን ሐሳብ በደምብ ለማጥናትና የት እንደሚገኝ ለማስታወስ ጥቅሙ ስለተረዳ የእንግሊዝ ካንተር በሪ ካርዲናል(ሊቀ ጳጳስ) ስቴቨን ላንግተን በ13ኛው ክ.ዘ. የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን በምዕራፍ  ከፋፈለው።ሶስት መቶ ዓመታት አለፍ ብሎም በ1551ዓ.ም ሮበርት ስቴፋነስ የተባለ ፈረንሳዊ በምዕራፍ ያሉትን ሙሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በቁጥር ከፋፈላቸው ይህም በምዕራፍ ውስጥ ያሉትን ሐይለ ቃላት ቶሎ ለማግኘት በጣም አጋዥ ሆነ።የእነዚህ ሁለት ሰዎች ስራ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለቤተ ክርስቲያን ትልቅ ውለታ ነው።ውለታቸውም በስነ መለኮት ትምህርት(theology)፣በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ከመጽሐፍ ቅዱስ እያጣቀሱ በሚጻፉ መጻህፍት እንዲሁም በሰባክያን ዘንድ የጀርባ አጥንት በመሆን በቤተ ክርስቲያን አሰራር ላይ የማይረሳና የማይቀየር የሚመሰገንም አሻራ ሆኗል። እግዚአብሔር የድካማቸውን ዋጋ    ይስጣቸው።

✨መጽሐፍ ቅዱስ የሰዎች ፈጠራ አለመሆኑና እውነተኛነቱ በምን ይታወቃል? ተብሎ ለቀረበው ጥያቄ፡-

☞በመጻሕፍቱ አንድነት ይታወቃል ይህም በተለያዩ ፀሐፊዎችና በተለያዩ ጊዜያት ውስጥ ቢፃፍም አንድ ሐሳብ አንድ ዓይነት ስሜት አላቸው።በዚህም አንዱ የእግዚአብሔር መንፈስ እንዳፃፋቸው እናውቃለን።

ስለ ነቢያቱ መጻሕፍት “21፤ ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ።”

(2ኛ የጴጥሮስ መልእክት 1:21፤)

በሐዋርያት ላይ መንፈስ ቅዱስ እንደሚሞላና እንደሚመራቸው እንጂ ከራሳቸው ፈጥረው እንደማይናገሩ

(የዮሐንስ ወንጌል 16)

———-

“13፤ ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤ የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤ የሚመጣውንም ይነግራችኋል።

14፤ እርሱ ያከብረኛል፥ ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋልና።

15፤ ለአብ ያለው ሁሉ የእኔ ነው፤ ስለዚህ። ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋል አልሁ። “

ደግሞም

(የዮሐንስ ወንጌል 15)

———-

“26፤ ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል፤

27፤ እናንተም ደግሞ ከመጀመሪያ ከእኔ ጋር ኖራችኋልና ትመሰክራላችሁ።”

✅ከዚህ እንደምንረዳው ነቢያቱን የመራውና የተናገረው የእግዚአብሔር መንፈስ፤ሐዋርያቱንም የመራና የተናገረው ነው ስለዚህ መጻሕፍቱ የሐሳብ አንድነት አላቸው ከእግዚአብሔር እንጂ ከሰው ፈቃድ እንዳልሆኑ እናውቃለን።

☞በተለይም በመጻሕፍቱ አንድነት ውስጥ የምናየው ስለ ክርስቶስ ያላቸው ምስክርነት ነው ለምሳሌ

ዘፍ፡-የሴቲቱ ዘር

ዘጸ፡-የፋሲካው በግ

ዘሌ፡-የመጨረሻው መስዋዕት

ዘኁ፡-የያዕቆብ ኮከብ

መዝ፡-መልካሙ እረኛ

ኢሳ፡-የሰላም አለቃ የዘላለም አምላክ የድንግል ልጅ

ኤር፡-የጽድቅ አምላክ

ዳን፡-የተቀባው(መሲሕ)

ሐጌ፡-የሁሉም ሕዝቦች ምኞት

ዘካ፡-የጌቶች ጌታ የአማልክት አምላክ

ሚል፡-የኪዳኑ መልእከተኛና የጽድቅ ፀሐይ

ማቴ፡-አማኑኤል የድንግል ልጅ

ማር፡-የእግዚአብሔር ልጅ፣የሰው ልጅ

ሉቃ፡-የመዳን ቀንድ

ዮሐ፡-ቃል፣የሕይወት ውሃ፣ትንሣኤና ሕይወት፣የዓለም ብርሃን፣የእግዚአብሔር በግ፣መልካሙ እረኛ

ሐዋ፡-የሚፈርደው

መልእክታት፡-ፋሲካችን፣የማዕዘን ድንጋይ፣የማይታይ አምላክ ምሳሌ፣አስታራቂ መስዋዕት፣በስጋ የተገለጠ

ራዕ፡-የይሁዳ አንበሳ፣አልፋና ኦሜጋ፣ፊተኛና ኋለኛ፣የሚያበራ የንጋት ኮከብ፣በብረት በትር የሚገዛ፣የአማልክት አምላክ የጌቶችም ጌታ፣የታመነው ምስክር ወዘተ

(የዮሐንስ ወንጌል 5)

———-

“46፤ ሙሴንስ ብታምኑት እኔን ባመናችሁ ነበር፤ እርሱ ስለ እኔ ጽፎአልና።

47፤ መጻሕፍትን ካላመናችሁ ግን ቃሌን እንዴት ታምናላችሁ?”

ስለዚህ በእግዚአብሔር መንፈስ ምሪት ስለተፃፉ የሐሳብ አንድነት ኣላቸው፡፡

(የሉቃስ ወንጌል 24)

———-

“44፤ እርሱም። ከእናንተ ጋር ሳለሁ በሙሴ ሕግና በነቢያት በመዝሙራትም ስለ እኔ የተጻፈው ሁሉ ይፈጸም ዘንድ ይገባል ብዬ የነገርኋችሁ ቃሌ ይህ ነው አላቸው።

45፤ በዚያን ጊዜም መጻሕፍትን ያስተውሉ ዘንድ አእምሮአቸውን ከፈተላቸው፤

46፤ እንዲህም አላቸው። ክርስቶስ መከራ ይቀበላል በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ይነሣል፥

47፤ በስሙም ንስሐና የኃጢአት ስርየት ከኢየሩሳሌም ጀምሮ በአሕዛብ ሁሉ ይሰበካል ተብሎ እንዲሁ ተጽፎአል።

48፤ እናንተም ለዚህ ምስክሮች ናችሁ።”

እንዳላቸው በወንጌልና በመልክታቸው ስለ ክርስቶስ ይመሰክራሉ፡፡ አጠር ባለ መልኩ ይህን ይመስላል።

☞የአሁኑ መጽሐፍ ቅዱስ ከድሮው በዘመን ሂደት ተበርዟል?

አልተበረዘም!!

መጽሐፍ ቅዱስ ሶስት ቅጂዎች ማለትም ዕብራይስጥ፣ ግሪክ፣ ሱርስት(ኣራማይክ) ቅጂዎች አሉት እነዚህ ቅጂዎች ቀዳሚ እንደ መሆናቸው በተለይም ግሪኩና ዕብራይስጡ ማመሳከሪያም ናቸው።በሌላ ቋንቋ ሲታተምም በነዚህ ሚዛንነት ነው።ወደ ሌላ ቋንቋ ተርጓሚው እንደ ትውልድ ቋንቋው ተናጋሪ(native speaker) ካልሆነ የትርጉም ክፍተት ሊፈጠር ይችላል።ከቀደምት መጻሕፍት ጋር በማስተያየት ግን በታተመው ላይ ያለው ልዩነት ይታወቃል።ስለዚህ እነዚህ ማመሳከሪያዎች ስላሉ ትርጉም ስራ ላይ የቃላት ለውጥ ቢፈጠር ይታረማል እንጂ ለመበረዝ ክፍተት የለውም።ጌታም እንዳለው ቃሉ ሕያውና የታመነ ነው አይሻርም አይበረዝም

“ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም” ማቴ24፥35

ክፍል አራት

🔐አጭር የጥናት መመሪያ🔐

መጽሐፍ ቅዱስ በሰዎች ቋንቋ እንደ መጻፉ እግዚአብሔር የጸሐፊዎቹን ቋንቋ፣ ባህል፣ የሚኖሩበት አካባቢ መልክዐ ምድራዊ አቀማመጥ፣ስነ ቃል ወዘተ ተጠቅሞ ስላፃፋቸው የመጽሐፉን ክፍል ስናጠና መጀመሪያ ስለፀሐፊው ማንነት ቀጥሎም የስነ ጽሑፉ ቅርፅ ባሕርይ(ዓይነት)፣ የሐገሩ ሰዋስው(አገባብ) ወዘተ መረዳት ያስፈልጋል።ለዛሬ በጥናት ጊዜ የሚጠቅሙን አንኳር ሐሳቦችን እንይ

1ኛ.መመልከት ፦ መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?

ግምታዊ አሰተሳሰብ ሳንሰጥ እንዲሁም ከሌሎች ወይም በስብከት የሰማነውን ትርጉም ቶሎ ሰጥተን አንለፍ ይልቅ ጥቅሶቹ በደምብ ሐሳባቸውን መረዳት “የተባለውን ነገር እውነት ይገልፃሉ?”ብሎ ማንበብ እንጂ ትርጉም ለመስጠት አለመቸኮል።ጸሐፊው በዚህ ክፍል ምን ማለት እንደፈለገ አንብበን በጥሞና መረዳት። በሚከትሉት ጥያቄዎችም በመደገፍ እውነቱን ማስተዋል ይገባል

★ባለታሪኮቹ እነማን ናቸው? ምን ተሰራ ምንስ ተደረገ? የት ቦታ በምንስ ሁኔታ? መቼ? እንዴት? ለምንስ? ውጤቱስ ምን ነበር? ምንስ ተፈጠረ?

የምናጠናውን ክፍል ከአውደንባቡ ለይተን ማውጣት የለብንም!!

★2ኛ.መተርጎም ፦ምን ማለቱ ነው? የሚለውን በመጠየቅ ፍቺ መስጠት። በአሁኑ ጊዜስ ተመሳሳይ የሆነው ፍቺው ምንድነው? መዝገበ ቃላት በመጠቀም ቃላቶቹን ፣ ሐረጎቹን፣ ቅኔያዊ አነጋገሮችንና ዐረፍተ ነገሮችን መተንተን

★3ኛ.ማዛመድ

ለምን ይህንን ሃሳብ ፣ ሐረግ፣ ቃል ተጠቀመ? ለምንስ ይህንን እዚህ መጥቀስ አስፈለገው? ያሉት የተለያዩ ሃሳቦችስ እንዴት ይዛመዳሉ?

ጠቃሚውን ሃሳብ ማግኘት።

ጎልቶ የሚታየውን መንፈሳዊ ሃሳብ ወይም መልዕክት ለይተን ማውጣት።ከሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶች ጋረ መስማማቱን ማረጋገጥ።

ዋናውን መልዕክት ቸል ብለን በጥቃቅን ነገሮች ላይ እንዳናተኩር ያልገባንን ለሌላ ጊዜ ጥናት ማስተላለፍ ወይም ሌሎችን በመጠየቅ መረዳት።

★4ኛ.የተለያዩ ሊቃውንት ትንታኔዎችን መመልከት

የአንዱን ሊቅ ሐሳብ ብቻ በመያዝ ትርጉም ሰጥቶ አይታለፍም!! ምክንያቱም በሊቃውንቱ አፈታት ወይም አተናተን ላይ መራቀቅ ሊኖር ይችላል ማለትም የአውደንባቡ ሐሳብ ሌላ ሊሆን ይችላል ነገር ግን በመራቀቅ እንዲህ ብለን ብንገልፀውም ያስኬዳል በሚል ንጽጽር ሐሳቡን ሊያሳዩን ይችላሉ።

★እዚህ ላይ ቅድሚያ ርቀ’ታዊ ሀሳቡ ሳይሆን የሚፈለገው ቀዳሚ አውደ ንባባዊ ትንታኔው ወይም ትርጉሙን ነው መጀመርያ የጸሐፊው(የነቢዩ ወይም የሐዋርያው) ሐሳብ ማግኘትና መረዳት ነው ያለብን። ስለዚህ ምክንያት የተለያዩ ትንታኔዎችን ማየት አለብን።አንዱ ሊቅ ምን ብሎ ተነተነው?ሌላውስ ምን አለ? ማእከላዊ (ሁሉንም ሊቃውንት የሚያቀራርበው) ትንታኔስ የትኛው ነው? በሚሉት ላይ በማተኮር ማጥናት።

እነዚህ ጠቅለልና አጠር ባለ መልኩ በጥናት ሂደት የሚጠቅሙን መመሪያዎች ናቸው።

በቀጣይ ክፍል ኦሪት ዘፍጥረት ትንታኔ እንጀምራለን

✞❀✞❀✞❀✞❀✞❀✞

“19፤ ደግሞ የወንጌልን ምሥጢር በግልጥ እንዳስታውቅ አፌን በመክፈት ቃል ይሰጠኝ ዘንድ ስለ እኔ ለምኑ፤”

(ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6:19፤)

✞❀✞❀✞❀✞❀✞❀✞

መዝሙረ ዳዊት 118(119)

“76. ምሕረትህ ለመጽናናቴ ትሁነኝ፥ እንደ ቃልህም ለባሪያህ ይሁነው።

  1. የቃልህ ፍቺ ያበራል፥ ሕፃናትንም አስተዋዮች ያደርጋል።

  2. አፌን ከፈትሁ፥ አለከለክሁም፤ ወደ ትእዛዝህ ናፍቄአለሁና።”

✞❀✞❀✞❀✞❀✞❀✞

“5፤ ቆማችሁ ከዘላለም እስከ ዘላለም አምላካችንን እግዚአብሔርን ባርኩ። እንዲህም በሉ። በበረከትና በምስጋና ሁሉ ላይ ከፍ ከፍ ያለው ክቡር ስምህ ይባረክ። “

(መጽሐፈ ነሀምያ 9:5፤)

አሜን!!

መጽሐፍ ቅዱስን ሰው ክቡር ቃሉን እንዳለ እንዲቀበል እንጂ ማንም እንደፈለገ እንዳያጣምመው ያስጠነቅቃል፡-

1ኛ) በሕግ (በሙሴ) መጽሐፍት፡- ዘዳ. 4፡2፤ 12፡32፤ 13፡1

2ኛ) በመዝሙራት፡- ምሳ. 30፡6

3ኛ) በነቢያት፡- ኤር. 26፡2

4ኛ) በወንጌል፡- ማቴ.5፡18-20

5ኛ) በሐዋርያት ሥራ፡- ሐዋ. 20፡29-31

6ኛ) በመልእክቶች፡- ገላ.1፡8፣9

7ኛ) በራእይ፡- ራእ. 22፡18-19

ክቡር የሆነውን ቃል፡- ተመልከት (ኤር.2፡31)፤ አንብብ (ኢሳ.34፡16) እንጂ፡-

(1) ከተጻፈው አትለፍ 1ቆሮ. 4፡6

(2) አትጨምር ወይም አታጉድል ራእ.22፡18-19፤ ዘዳ. 4፡2፤

(3) አታጣምም 2ጴጥ. 3፡15-16 

(4) ለራስህ አትተርጉም 2ጴጥ. 1፡20

(5) አትግፋ ሐዋ. 7፡38-39

(6) አትናቅ ሐዋ. 13፡40፤ ዕባቆ. 1፡5

(7) አታወላውል ኢያ.1፡7-8   

(8) አትሻር ማቴ. 5፡19        

(9) አትስረቅ ኤር. 23፡30

(10)  ከራስህ ልብ አትናገር ኤር.23፡16

(11) በውሸት አትቀላቅል 2ቆሮ.4፡1-3

(12) አንዲትም ቃል አታስቀር ኢያሱ 8፡35

አራቱ ወንጌላት(ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ፣ ዮሐንስ)

ወንጌል የሚለው ቃል ትርጉም፦ በግእዝና በአማርኛ <ወንጌል> የምንለው ቃል ትርጉም፦ ብስራት፣ ስብከት፣ የምሥራች ማለት ነው። ይህ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ተገልጦ ከመታየቱ በፊት በግሪክ ቋንቋ
ለሚወዱት ሰው የምሥራች ተብሎ የሚሰጥ የደስታ መግለጫ የሆነ መልካም ስጦታን ያመለክት ነበር። ከክርስቶስ ልደት በኋላ ግን ወንጌል የሚለው ቃል በክርስትና እምነት በተለይም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሲነገር የሚከተሉትን ሁኔታዎች ያመለክታል።
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የተናገረው ወይም ያስተማረው መልካም የምስራች ነው። ስለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚነገረው መልካም የምሥራች ዜና ሠናይ ነው። ትምህርቱንም <ወንጌል> ብሎ ለመጀመሪያ ጌዜ የጠራው ራሱ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ወንጌል ማለት የምስራች ወይም መልካም ዜና ለመሆኑ ተከታዩን የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባብ አምላካችን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን መመልከት ያስፈልጋል፦
ኢየሱስ ክርስቶስ በትምህርቱ፦
􀂾 ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል። ማቴ. ፳፬፡፲፬
􀂾 እውነት እላችኋለሁ ይህ ወንጌል በዓለም ሁሉ በማናቸውም ስፍራ በሚሰበክበት እርስዋ ያደረገችው ደግሞ ለእርስዋ መታሰቢያ እንዲሆን ይነገራል። ማቴ. ፳፮፡፲፫
􀂾 ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ። ማር. ፲፮፡፲፭ ያለ ሲሆን ከጌታችን ቀጥሎም ሐዋርያትና የጌታ ደቀመዛሙርት ሁሉ ስለኢየሱስ ክርስቶስ የሚሰብኩትንና የሚጽፉትን <ወንጌል> ብለው ጠርተውታል።
ወንጌላዊው ማቴዎስ፦
􀂾 ኢየሱስም በምኩራቦቻቸው እያስተማረ የመንግሥትንም ወንጌል እየሰበከ በገሊላ ሁሉ ይዞር ነበር። ማቴ. ፬፡፳፫
􀂾 ኢየሱስም በምኩራቦቻቸው እያስተማረ የመንግሥትንም ወንጌል እየሰበከ በሕዝብም ያለውን ደዌና ሕማም ሁሉ….ተጨማሪ ያንብቡ ︾

መጽሐፍ ቅዱስ በኢትዮጵያ፡-

– ብሉይ ኪዳን በሐገራችን ቋንቋ በግዕዝ የተተረጎመው ከክርስቶስ ልደት በፊት አንድ ሺህ ዓመት ቀደም ብሎ ሲሆን ይኸውም በንግሥተ ሳባ ዘመነ መንግሥት ጊዜ ነው፡፡

– ኢትዮጵያ ከዚህን ጊዜ ጀምሮ መጻሕፍትን ጠብቃ አቆይታለች፡፡ አባቶች ምንም አይነት ጦርነት ቢነሳ ህይወታቸውን በማስቀደም መጻሕፍትን ጠብቀው አቆይተውልናል፡፡

– ከምዕራባውያን በፊት ክርስትናን ሆነ የአይሁድ እምነትን የተቀበለችው ሀገራችን በምዕራባውያን የሌሉ መጻሐፍት መገኛ ብቸኛ ሀገር ናት፡፡ ለዚህም ነው በአይሁድ ዘንድ ሆነ በሮማውያን ዘንድ በነበረው ጦርነት የጠፉ መጻህፍት ኢትዮጵያ ውስጥ ግን የሚገኙት፡፡ ለዚህም መጽሐፈ ሄኖክ እና መጽሐፈ ኩፋሌ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ የመጽሐፈ ሄኖክ ጥቅልል አሁን በቅርቡ በቁምራን ዋሻ ተገኝቷል፡፡ የተገኘው ጥቅልልም ሀገራችን ጠብቃ ካቆየችው መጽሐፈ ሄኖክ ጋር አንድ አይነት ሆኖ በመገኘቱ ምዕራባውያን ተርጉመው መጠቀም ጀምረዋል፡፡

 

-+- የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት:-

– የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ሁለት አይነት የቀኖና ክፍሎችን ያካትታል እነሱም ፕሮቶካኒካል እና ዲዩትሮካኖኒካል ይባላሉ፡፡

– (የመጀመሪያ)፡- እነዚህ መጻሕፍት የተሰበሰቡት በካህኑ እዝራ ሲሆን መጀመሪያ በቀኖና መጻሕፍትነት የተመዘገቡ ናቸው፡፡ 1ኛ. መቃብያን 2፡10 “ነህምያም የነገስትን መጻሕፍት የያዘ ቤተ መጻሕፍት አቋቁሞ ነበር“ እነዚህም መጻሕፍት በ ሶስት ይከፈላሉ እነሱም ቶራህ (አምስቱ ብሔረ ኦሪት) ፣ ነበኢም (ቀደምት ነብያት እና ደኃርት ነብያት) እና ከተቢም (ታላላቅ የታሪክ መጽሐፍትና ታናናሽ የታሪክ መጽሐፍትን ያካትታል) ተብለው ይጠራሉ፡፡ እንዲሁም

– ዲዩትሮካኖኒካል የምንላቸው አይሁድ እንደ ቀኖና መጻሕፍት የማይቀበሉዋቸው ግን እንደ አዋልድ መጻህፍት የሚቀበሉዋቸው ናቸው፡፡ በነገራችን ላይ

-> አይሁዶች 24 የብሉይ ኪዳን መጻህፍትን ብቻ ሲቀበሉ (የመጽሐፋቸው አቆጣጠር ከእኛ አቆጣጠር ይለያል)

-> ፕሮቴስታንቶች 39 የብሉይ ኪዳን እንዲሁም 27 የሐዲስ ኪዳን ይቀበላሉ፡፡

-> ካቶሊኮች 46 የብሉይ ኪዳን መጻህፍት እና 27 የሐዲስ ኪዳን መጻህፍት ሲቀበሉ እኛ

-> ኦርቶዶክስ ተዋህዶዎች ግን 46 የብሉይ ኪዳን እና 35 የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት እንቀበላለን፡፡ (ከካቶሊኮች ጋር በብሉይ ኪዳን የምንቀበላቸው መጻሕፍት ላይ የአቆጣጠር እና የመጻሕፍት ልዩነት አለ፡፡)

– እዚህ ላይ ከላይ በግልጽ እንደምንረዳው 81 የነበረው የመጀመሪያው መጽሐፍ ቅዱስ ብዛት ቀስ በቀስ በሰዎች እየተቀነሰ እንዲሁም በነበሩት ጦርነቶች መጻሐፍቱ እየጠፉ በመምጣታቸው፣ መጀመሪያ 73 እንዲሆን በመቀጠልም ማርቲን ሉተር ሲያምንበት ከነበረው የካቶሊክ እምነት ፣ከካቶሊክ መነኮሳት ጋር በነበረው የግል ጸብ እና የፖለቲካ ጸብ (የጀርመን ዜጋ ስለነበር የአይሁዶች ጥላቻ ስለነበረው) በነበረው ቅራኔ ምክንያት 7 መጻህፍትን በገዛ ፈቃዱ ቀንሶ ዛሬ በምዕራብውያን ዘንድ በስፋት የተስፋፋውን እና የእኛን ሐገር ጨምሮ በኢኮኖሚ እና በፖለቲካ ሀይል የሌላቸውን ሀገራት የተቆጣጠረውን የ66 መጻሐፍት ሊያስፋፋ ችሏል፡፡

 

።–> መናፍቃን 81 /ሰማንያ አሃዱ/ መጽሐፍ ቅዱስን የማይቀበሉባቸው ምክንያቶች እና እንዲቀበሉ የሚያስገድዳቸው ምክንያቶች እንዲሁም ከስልሣ ስድስቱ ውጭ ሌሎች ቅዱሳት መጽሐፍት የሉም እንዳይሉ ማስረጃዎች፡-

-> ተቃዋሚዎች ከ66 ውጭ መጽሐፍ የለም ቢሉም ሐዋርያት ሆኑ ጌታ ከ81 መጻሐፍት እየጠቀሱ አስተምረዋል፡፡ ይህን እስቲ በማስረጃ እንመልከተው፡፡

 

_ማስረጃ 1. – ኢየሱስም ሊያስተምር ሲጀምር ዕድሜው ሠላሳ ዓመት ያህል ሆኖት ነበር ይለናል ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ (ሉቃ.3፡3) – እንግዲህ ጌታችን አምላካችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከ30 ዓመቱ በፊት የት ነበረ? ምን እየሰራ ነበረ? ብልን ስንጠይቅ መልሱን በ66 መጻሕፍት ውስጥ ሳይሆን በቤተክርስቲያናችን የትውፊት መጻህፍት ውስጥ እድገቱምን እንደሚመስል በዝርዝር ተጽፎ እናገኛለን፡፡

 

_ማስረጃ 2. – በማቴዎስ ወንጌል 27፡3-10 (በዚያን ጊዜ አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ እንደ ተፈረደበት አይቶ ተጸጸተ፥ ሠላሳውንም ብር ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች መልሶ፦ ንጹሕ ደም አሳልፌ በመስጠቴ በድያለሁ አለ። እነርሱ ግን። እኛስ ምን አግዶን? አንተው ተጠንቀቅ አሉ። ብሩንም በቤተ መቅደስ ጥሎ ሄደና ታንቆ ሞተ። የካህናት አለቆችም ብሩን አንሥተው። የደም ዋጋ ነውና ወደ መባ ልንጨምረው አልተፈቀደም አሉ። ተማክረውም የሸክላ ሠሪውን መሬት ለእንግዶች መቃብር ገዙበት። ስለዚህ ያ መሬት እስከ ዛሬ ድረስ የደም መሬት ተባለ። በዚያን ጊዜ በነቢዩ በኤርምያስ የተባለው። ከእስራኤል ልጆችም አንዳንዶቹ የገመቱትን፥ የተገመተውን ዋጋ ሠላሳ ብር ያዙ፥ ጌታም እንዳዘዘኝ ስለ ሸክላ ሠሪ መሬት ሰጡት። የሚል ተፈጸመ።) በዚያን ጊዜ የነቢዩ የኤርሚያስ ቃል ተፈጸመ ይለናል ይሁዳ… እንዲህ ያለው ‹‹የእስራኤል ልጆች የተስማሙበትን የክቡርን ዋጋ ሠላሳውን ብር ወሰዱ›› ይህን ቃል የምናገኘው በስድሳ ስድስቱ ውስጥ ሳይሆን በተረፈ ኤርሚስ 7፡ 2-4 ባለው ላይ ነው፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ ትንቢተ ኤርሚያስን ጠቅሶ ሲጽፍልን ‘በነብዩ ኤርሚያስ የተባለው ብሎን ነው፡፡’ ምን ተባለ ስንል ማቴዎስ ”የተባለውን” እና ”ተፈጸመ” ያለንን የምናገኘው መናፍቃኑ አንቀበለውም በሚሉት በ81 መጽሐፍት ውስጥ ነው፡፡

 

_ማስረጃ 3. – ኦሪት ዘፍጥረት 1፡26 እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር፡፡ ‹‹እንፍጠር›› ሲል ከአንድ በላይ ብዛትን ሲያመለክት 2 ወይም 4 ወይም 10 ሳይሆኑ ስላሴን /ሶስትነት/ ስስት መሆናቸውን የሚነግረን በሲራክ 2፤22 ሄኖክ 5፤38 ሄኖክ 6፤24 ሄኖክ 13፤14 እዝራ ስቱኤል 4፤56 እዝራ ስቱኤል 12፤48 ሲራክ 44፤10 በግልጽ ሥላሴ እያለ በማሳየት ነው፡፡ ክብር ለቅድስት ሥላሴ ይሁን!

 

ማስረጃ 4. በሉቃስ 14:13-14 “ነገር ግን ግብዣ ባደረግህ ጊዜ ድሆችንና ጕንድሾችን አንካሶችንም ዕውሮችንም ጥራ፤ የሚመልሱት ብድራት የላቸውምና ብፁዕ ትሆናለህ” የሚለውን ኃይለ ቃል ከጦቢት 4፡7፡10 የተገኘ ነው ‹‹ከገንዘብህም ምጽዋት ስጥ ምጽዋትም በመጸወትህ ጊዜ በገንዘብህ አትዘን፣ ከድሃም ፊትህን አትመልስ፤ እግዚአብሔርም ገጸ በረከቱን ካንተ አይመልስም፡፡››

 

_ማስረጃ 5. 1ኛ ወደ ተሰሎንቄ ሰዎች 4፡2 በጌታ በኢየሱስ የትኛውን ትእዛዝ እንደ ሰጠናችሁ ታውቃላችሁና። ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ እርሱም መቀደሳችሁ ነውና፤ ከዝሙት እንድትርቁ፥ የሚለውን ኃይለ ቃል ቅዱስ ጳውሎስ ከጦቢት 4፡12 ጠቅሶ ነው ያስተማረው የተገኘ ነው፡፡

 

_ማስረጃ 6. በዮሐንስ ወንጌል 10፡22 በኢየሩሳሌምም የመቅደስ መታደስ በዓል ሆነ፤ … ‹‹የመቅደስ መታደስ በዓል›› በሌሎቹ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት አናገኘውም ግን ቅዱስ ዮሐንስ ከመጽሐፈ መቃብያን 4 ላይ ጠቅሶ ተናገረ፡፡

 

_ማስረጃ 7. በ ሮሜ 13፡1 ከእግዚአብሔር ካልተገኘ በቀር ሥልጣን የለምና፤ ያሉትም ባለ ሥልጣኖች በእግዚአብሔር የተሾሙ ናቸው። የሚለው ኃይለ ቃል ከሲራክ 17፡14 የተወሰደ ነው፡፡

 

_ማስረጃ 8. አዳምና ሔዋን አቤልና ቃየልን ወለዱ፡፡ ቃየል ሚስቱን አወቀ ጸነሰችም ይላል ዘፍጥረት 4፡17 በ66ቱ መጽሐፍት ላይ ስለ አቤልና ቃየል መወለድ እንጂ ሌላ የሰው ዘር በምድር ላይ ሰለመኖራቸው ምንም አያወራም፡፡ ታድያ ይህቺ የቃየል ሚስት ከየት መጣች? ስለስዋ ምንም አይናገርም በአለም ላይ የነበሩ ሰዎች አራት ብቻ እንደነበሩ ነበር የምናነበው፡፡ የዚህን መልስ የምናገኘው በኩፋሌ 5፡8-17 ላይ ነው፡፡

 

_ማስረጃ 9. – ይሁዳ በመልዕክቱ ‹‹የሄኖክን ትንቢት ከመጽሐፈ ሄኖክ ጠቅሶ›› ጽፎታል (ከአዳም ጀምሮ ሰባተኛ የሆነ ሄኖክ። እነሆ፥ ጌታ በሁሉ ላይ እንዲፈርድ፥ በኃጢአተኝነትም ስላደረጉት ስለ ኃጢአተኛ ሥራቸው ሁሉ ዓመፀኞችም ኃጢአተኞች በእርሱ ላይ ስለ ተናገሩ ስለ ጭከና ነገር ሁሉ ኃጢአተኞችን ሁሉ እንዲወቅስ ከአእላፋት ቅዱሳኑ ጋር መጥቶአል (ይሁዳ 1፡14-15) መጽሐፈ ሄኖክ ደግሞ በስልሣ ስድስቱ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የለም፡፡ ሄኖክ ትንቢት ተናገረ ብሎ ከትንቢቱ ጠቅሱ ይሁዳ በመልዕክቱ ጽፎልናል ይህም ትንቢት በሄኖክ 1፡9 ላይ በግልጹ ተቀምጦ እናገኘዋለን፡፡ እንግዲህ ይሁዳ ሄኖክ ትንቢት መናገሩን እየነገረን ተቃዋሚዎች ሄኖክ ትንቢት አልተናገረም ይሉናል፡፡እኛስ በመንፈስ ቅዱስ ተመርቶ የጻፈወን ይሁዳን እናምናለን፡፡ እሱ የተቀበለውን እንቀበላለን ጥበብ አይኮረጅም (መጽሐፍ ቅዱስ ትውፊታዊ የአምላክ ቃል)

ማስረጃ 10.
❀1ኛ ቆሮ. 10፡9 ‹‹ከእነርሱም አንዳንዶቹ ጌታን እንደ ተፈታተኑት በእባቦቹም እንደ ጠፉ ጌታን አንፈታተን›› የሚለው ቃል ከዮዲት 8፡24 የተገኘ ቃል ነው፡፡

-+- በመጀመሪያ እስኪ መጽሐፍ ቅዱስ ትውፊታዊ መረጃ መሆኑን እንተማመን፡፡ ትውፊት ማለት ቅብብል፣ ርክክብ ወይም ውርስ ማለት ነው፡፡ ይህ መንፈሳዊ ውርስ ከቀደሙት አበው ለእኛ በርክክብ ደርሶናል፡፡ አንዱ ከሌላው የተቀበለውን ለሌላው አሳልፎ በመስጠት እስከ ዘመናችን የደረሰ እውነታ ነው፡፡ ትውፊት መጽሐፍ ቅዱስ ከመጻፉ በፊት ያለ የነበረ ነው፡፡ እንደውም መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚሐብሔር ቃል መሆኑን አምነን የተቀበልነው የቀደሙት አባቶቻችን የእግዚሐብሔር ቃል መሆኑን በትውፊት ስላስረዱን ነው፡፡

-ለምሳሌ፡-

1-ዓለም ከተፈጠረ ሺህ 486 ዘምን መጽሐፈ ሄኖክ ተጻፈ

2- እስራሄል በግብጽ ሳሉ በፈርሆን ዘመን የኢዮብ መጽሐፍ ተጻፈ

3- 3643 ዓ.ዓ. እስራሄል ከግብጽ ወጡ በዚህ ጊዜ ኦሪት ተጻፈ፣ ወዘተ. . . . . እንግዲህ ከ1486 ዘመን በፊት የተጻፈ ህግ አልነበረም፤ በዚያ ጊዜ የነበሩ አበው ይመሩ የነበሩት ሙሉ በሙሉ በትውፊት ወይም በህገ ልቡና ነበር ማለት ነው፡፡ ከስልሳ ስድስቱ (66) መጽሐፍ ቅዱስ ውጪ ሌሎች ቅዱሳት መጻህፍትየለም የምትሉ ወይም ትውፊታዊ መረጃ አንቀበልም ለምትሉ እስኪ የሚከተለውን ጥያቄ ላቅርብ

 

1- በኦሪት ዘፍጥረት አገላለጥ ቃየንም ሆነ አቤል ሁለቱም ለእግዚሐብሔር ከስራቸው ውጤት መስዋዕት አቅርዋል፡፡ ዳሩ ግን የተቀበለው የአቤልን መስዋዕት ብቻ ነው፡፡ የቃየንን መስዋዕት ያልተቀበለው ለምንድን ነው? መቼም ለአቤል አድልቶ ነው የሚል መልስ እንደማይሰጥ እርግጣኛ ነኝ ምክንያቱም እግዚሐብሔር ለሰው ፊት አያዳላም፡፡

2- አቤል ከበጎቹ በኩራትና ከሰቡ እግዚሐብሔር መስዋእት አቅርቧል፤ ከበጎቹ መካከል በኩራትና ስቡን ማቅረብ እንደሚገባ እንዴት አወቀ? ምክንያቱም የጽሁፍ ህግና ትዕዛዝ በዘመኑ አልነበረም

3- ‹ቃየንም ሚስቱን አወቀ ጸነሰችም ሄኖህንምም ወለደች› ይላል፡፡ እግዚሐብሔርወንድና ሴት አድርጎ የፈጠረው አዳምንና ሄዋንን ብቻ ነው፡፡ አዳምና ሄዋን ደግሞ የወለዱአቸው አቤልና ቃየንን እንደሆነ በምዕራፍ 4 ተገልጽዋል ፤ታዲያ የቃየን ሚስት ማንነች? ከየትስ መጣች? ስለሆነም ከላይ የተጠቀሱትን ጥያቄዎች ለመመለስ ከ66 መጽሐፍ ቅዱስ ውጭ የሆኑትን ሌሎች ቅዱሳት መጻህፍትንና ትውፍታዊ መረጃ መሰረት ማድረግ ይገባል ያለበለዚያ ጥያቄዎቹ የማይፈቱ እንቆቅልሽ ሆነው መቅረታቸው ነው?

 

– እስኪ ደግሞ ወደ ሐዲስ ኪዳን እንሂድ፡፡ የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ቢያንስ ቢያንስ ለ20 ዓመታት ያህል ስለ ጌታ ይማሩ የነበሩት በቃል ነበር ምክያቱም ሐዲስ ኪዳን ገና በጽሁፍ አልተቀረጸም ነበርና በቅብብል ወይም በሰሚ ያገኙትንም እነርሱ ራሳቸው ከጌታ እደተቀበሉት አድርገው ያስተምሩ ነበር ለዚህም ጥሩ ምሳሌ የሚሆነው ጳውሎስ ነው (1 ቆሮ. 11፥23-24)፡፡ ጳውሎስ ከሐዋርያት ቃል የተማረውን ለሌሎች ደግሞ አስተላለፈ፡፡ ስለዚህም ወንጌል የሚያሰኘው በጽሁፍ መስፈሩ ብቻ ሳይሆን የሕያው የእግዚሐብሔር ቃልና የህይወት መንገድ መሆኑነው፡፡ በጌታ ጊዜ ወንጌል ገና አልተጻፈም ነበር፣ “ለሐዋርያቱም ወደ ዓለም ሒዱ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ ”(ማር.16፥1) ይህም ሲል የሰሙት ተማሩት እንጂ በጽሁፍ ቀርጾ የሰጣቸው ወንጌል አልነበረም፡፡

_ በተጨማሪም በማርቆስ ወንጌል ም.1፥21-22 ‹ወደ ቅፍራንሆም ገቡ ወዲያውም በሰንበት ወደ ምኩራብ ገብቶ አስተማረ እንደ ባለስልጣን ያስተምራቸው ነበር እንጂ እንደ ጸፎች አይደለምና በትምህርቱ ተገረሙ›፡፡ ይህ የክርስቶስን ተቃዋሚዎች ራሱ ያስገረማቸው ትምህርት ምን አይነት ነበር ‹ከሙሴና ከነቢያት ሁሉ ጀምሮ ስለእርሱ በመጻህፍት ሁሉ የተጻፈውን ተረጎመላቸው› ሉቃ 24-27

_ ከትንሳሄው በኋላ ለሁለቱ ደቀ መዝሙር ተረጎመላቸው የመጻህፍት ትርጓሜ በየትኛው ሀዲስ ኪዳን ላይ ይገኛል? “በነቢያት ናዝራዊ ይባላል የተባለው ይፈጸም ዘንድ. . . ናዝሬት ወደምትባል ከተማ መጥቶ ኖረ” ማቴ 2፥23 ይህን የተናገረው ነቢይ ማነው? በየትኛው የትንቢት መጽሐፍ ይገኛል? ማቴ 27፥9 ‹በዚያን ጊዜ በነቢዩ ኤርምያስ የተባለው ከእስራሄል ልጆችም አንዳንዶቹ የገመቱትን የተገመተውን ዋጋ ሰላሳ ብር ያዙ ጌታም እንዳዘዘኝ ስለ ሸክላ ሰሪ መሬት ሰጡት የሚል ተፈጸመ› ይህስ ከየት ተገኘ? በተጨማሪም ሉቃ 2፥25-32፣ 2ኛ ጢሞ 2፥ 8፣ ዕብ 12፥ 21 ፣ ራዕይ 2 ፥14፣ ዮሐ 20፥ 30 ፣ ዮሐ 21 ፥25፣ ይሁዳ 9 እንዲሁም ዮሐ 1 ፥48 ሌሎች ማሳያዎች ናቸው፡፡

_ በአጠቃላይ እነዚህ መረጃዎች ከ66ቱ መጻህፍት የማናገኛቸውና ነገር ግን ተዋህዶ እምነት በምትጠቀምበት ሰማንያ አህዱ ውስጥ ፍንትው ብለው የተጠቀሱ ናቸው፡፡ ታዲያ እነዚህን የመሳሰሉ ፍሬ ሃሳቦች ስለተቀመጡበት ነው ሰማንያ አሃዱን ከሌላው ጋር ይጋጫል የሚባለው?

_ ብርሃን ዓለም ጳውሎስ ‹እንግዲያስ ወንድሞች ሆይ ጸንታችሁ ቁሙ በቃላችንም ቢሆን ወይም በመልእክታችን የተማራችሁትን ወግ ያዙ› ያለው (2ተኛ ተሰሎንቄ 2 15)፡፡ በቃላችንም በመልእክታችንም የተማራችሁትን ‹ወግ› ያዙ ሲል ትውፊትን ማለቱ ነው፡፡

_ ፊልጵ 4፥9 ‹ከህኔ የተማራችሁትና የተቀበላችሁትን የሰማችሁትንም እና ያያችሁትንም እነዚህን አድርጉ የሰላምም አምላክ ከእናንተ ጋር ይሆናል›፡፡ የቅዱስ ጳውሎሰ መልዕክት ግልጽ ነው፡፡ በፊልጵስዮስ የሚኖሩ ክርስቲያኖች ከእርሱ ከአንደበቱ የተማሩትንና በጽሁፍ የተቀበሉትንም የሰሙትንም ያዩትንም ሁሉ እንዲይዙ እንደያደርጉ እንጂ የተጻፈውን ብቻ እንዲይዙና እንዲጠብቅ አልነበረም፡፡ ዛሬም እኛ በትውፊት የደረሰንን ሁሉ ልንጠብቅ መንፈሳዊ ግዴታችን ነው ፡፡

_ 2ኛ ጢሞ ‹የእግዚሐብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ስራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ የእግዚሐብሔር መንፈስ ያለበትን መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሳጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ይጠቅማል›፡፡ ምክሩም ጠቃሚና አስፈላጊ መሆኑን ተዋህዶዋውያን እናምናለን፡፡ ስለዚህም በቤተክርስቲያናችን ያሉትን የእግዚሐብሔር መንፈስ ያለባቸውን ቅዱሳት መጻህፍት ሁሉ ለክርስቲያናዊ ህይወታችን እንገለገልባቸዋለን፡፡

–> በመጨረሻም ኦርቶዶክሳዊያን በቤታችን ያለን መጽሐፍ ቅዱስ:-

81: የኦርቶዶክስ

73: የካቶሊክ

66: የፕሮቴስታንት

24: የአይሁድ

በሆኑንና አለመሆኑን ለይተን ተረድተን የረሳችንን የሆነውን ትክክለኛውን 81 አሐዱ መጽሐፍ ቅዱስን እንጠቀም።

ዳውንሎድ ሞባይል አፕ

ሶሻል ሚድያ ላይ ያግኙን

 

Copyright © 2010 – 2023 zetewahedo.com | All rights reserved.
error: Content is protected !!
Scroll to Top